Monday, 23 June 2014

የግንቦት 20 ጫፍ አልባ ቁልቁለቶች-2

ኢኮኖሚ እንደ ‹‹ሸንበቆ›› ህዝብ እንደ ሙቀጫ

ለመሆኑ መንግስት ስለሚያወራው ኢኮኖሚ ህዝቡ ምን ያክል ገብቶታል? ህዝቡስ ከእድገቱ ምን አተረፈ? ማነው ያደገው? እንዴት ነው ያደገው? የሚሉት እና የመሳሰሉት ጥያቄዎች ዘወትር ወደ ጭንቅላቴ እየመጡ እረፍት ይነሱኛል፡፡ መንግስት እና ህዝብ በቀጥታ ቀርቶ በአስተርጓሚ እንኳ መግባቢያ ቋንቋ ካጡበት ዘርፍ ዋነኛው እንደ ሸንበቆ እያደገ ነው የተባለለት እንዲሁም ሃገራዊ ፍቅርን፣ ህዝባዊ ክብርን፣ ዲሞክራሲን፣ ፍትህን፣ ነፃነትን እና የህዝቦችን የመኖር ህልውን እንደ ሙቀጫ ቁልቁል ያንከባለለውን የኢኮኖሚ ስርዓት በዚህ አጭር ፅሁፍ ለመዳሰስ እሞክራለው፡፡
ህዝብ እና መንግስት አንድ ቋንቋ መናገር አልቻሉም፡፡ የመንግስት ቋንቋ ገብቶናል ያሉት ሃገር በቀል እና የውጪ የመንግስት አፈ ቀላጤዎችም ህዝቡ በሚገባው ቋንቋ መናገር ተስኗቸው ማሳመን (convince) ባይሳካላቸውም ማደራገር (confuse) በጥቂቱም ቢሆን እየተሳካላቸው ይገኛል፡፡

ህዝብ ዘወትር እየተመነጠቀ ስላለው የኑሮ ውድነት ሲያወራ መንግስት ስለ ‹‹ባለሁለት አሃዙ›› እድገት ያወራል፡፡ ህዝብ ስለ ስራ-አጥነት ሲያወራ መንግስት ‹‹ስለኢንቨስትመንት መስፋፋት›› ይደሰኩራል፡፡ ህዝብ ስለረሃብ መንግስት ‹‹ስለጥጋብ››፤ ህዝብ ስለዳቦ መንግስት ‹‹ስለመሰረተ ልማት›› እያወሩ መግባባት ተስኗቸው 23 አመት ያላቻ ጋብቻ በዓላቸውን አንዱ የደስታ ሌላኛው የሃዘን ሻማ በማብራት አክብረው አሳልፈዋል፡፡ ከእንደዚህ አይነት ስርዓት አልባ ስርዓት ጋር ፍቺ ብቸኛ አማራጭ ነው፡፡  

ሃገርን ለመምራት ከተፈለገ ከህዝብ ጋር አንድ ቋንቋ መነጋገር ያስፈልጋል፡፡ ቋንቋ ሲባል አማርኛ፣ ኦሮምኛ ወይ ትግርኛ አለያም ወላይትኛ ወይም አፋርኛ ወይ ደግሞ ሱማልኛ … ወ.ዘ.ተ ማለት ሳይሆን ህዝብ የሚለውን መንግስት መስማት አለበት፡፡ መሪነት ከህዝብ ጋር መግባባት ማለት ነው፡፡ ከህዝብ ጋር መግባባት ሳይኖር ሲቀር ገዢነት ይፈጠራል፡፡ አሁን ያለው ስርዓት አምባገነን የገዢነት ስርዓት ነው የሚባለውም ህዝብ የሚለውን መንግስት መስማት ስለተሳነው እና የህዝብን ጥያቄ በተቃራኒው በመመለሱ ማለትም ህዝብ ኑሮ ተወደደብኝ ወይም ራበኝ ሲል የመንግስት መልስ ገበሬውን ከእርሻው በማፈናቀል፣ የማዳበሪያ እና የዘር ዋጋን በማናር ገበሬው እንዳያመርት ወይም ያመረተውን በተመጣጣኝ ዋጋ እንዳይሸጥ በማድረግ ገቢያውን ከማረጋጋት ይልቅ ችግሩን ከድጡ ወደ ማጡ ማስገባቱ ነው፡፡

በአንድ ሃገር የምጣኔ ሃብት (የኢኮኖሚ) እድገት አለ ለማለት በትንሹ የህዝቦች መሰረታዊ ፍላጎት ተሟልቶ በሃገራቸው የመኖር ዋስትናቸው መረጋገጥ ይኖርበታል፡፡ የምጣኔ ሃብት እድገት እና የህዝቦች የመኖር ህልውና በቀጥተኛ መንገድ የተያያዙ ናቸው፡፡ በአንድ ሃገር የኢኮኖሚ እድገት እየተመዘገበ ነው ማለት የህዝቦች በሃገራቸው የመኖር ህልውናቸውም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻለ ነው ማለት ነው፡፡ ታዲያ መሬት ላይ ያለው እውነታ (facts on the ground) ይህንን ይነግረናል?


በሃገሪቷ ውስጥ ያለው የምጣኔ ሃብት እድገት አለ ለማለት ህዝቦች ቢያንስ ያለ ምንም ልዩነት መሰረታዊ ፍላጎቶች ተብለው የሚጠሩትን ማለትም ምግብ፣ አልባሳት እና መጠለያ ለማግኘት የሚጓዙት መንገድ ምን ያክል ከትላንት ዛሬ እንዳጠረ ብቻ መመልከት ተገቢ ነው፡፡ ለስርዓት አልባው ስርዓት ቅርብ ወይም የገዢው መደብ አባላት ካልሆኑ በስተቀር ዛሬ ላይ ቆመን እነዚህ ነገሮች የማያስጨንቁት የህብረተሰብ አካል አለ ብሎ ለማሰብ በማይቻልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል፡፡
የልጆች ምግብ እና አልባሳት የማያስጨንቀው ቤተሰብ ወይም አሳዳጊ እንዲሁም የመጠለያ ችግር የማያማርረው ዜጋ ማግኘት ከጭድ ክምር ውስጥ መርፌ የማግኘት ያህል ከባድ ከሆነብን እነሆ ሁለት አስርት አመታትን አሳልፈናል፡፡ ታዲያ ከገዢው መደብ አባላት ውጪ የህዝቦችን መሰረታዊ ፍላጎት በትንሹ እንኳ ማሟላት ያልቻለው የምጣኔ ሃብት እድገት ምን ማለት ነው?

በአንድ ሃገር ያለው የምጣኔ ሃብት እድገት በባለስልጣናት ኪስ ወይም በድንጋይ ቁልል ወይም ንጣፍ መለካት ተገቢ ሊሆን አይችልም፡፡ ጣሊያን ኢትዮጵያን ለአምስት አመታት ስትገዛ የባንዳዎችን (የባለስልጣናትን) ኪስ አደልባለች እንዲሁም አሁንም ድረስ ለምስክርነት የቆሙ መንገዶችን ህንፃዎችን ገንብታለች ነገር ግን ህዝቦች በሃገራቸው በነፃነትና በሰላም የመኖር መብታቸውን ነፍጋለች፡፡ ጣሊያን የነፈገቻቸው የህዝቦች በሃራቸው እንደ ሰው በሰላም እና በነፃነት የመኖር መብታቸው ከሰራቻቸው የመሰረተ ልማት መስፋፋት ጋር ማወዳደር ለማንም ኢትዮጵያዊ የማይዋጥ ነው፡፡ ታዲያ ይሄ ስርዓት ከዚህ የተለየ ምን አደረገ?

በአንድ ሃገር ያለ የምጣኔ ሃብት እድገት መለካት ያለበት በህዝብ የኑሮ መሻሻል ነው፡፡ የህዝቦች በሃገራቸው በክብር፣ በሰላም እና በነፃነት የመኖር ዋስትናቸው በምን ያክል ተረጋግጧል?
ይህንን ጥያቄ ለመመለስ ዜጎች በሃገራቸው ሰርተው መሰረታዊ ፍላጎታቸው ማሟላት ተስኗቸው ብሎም በአያት በቅድመ አያታቸው መሬት በሰላም፣ በክብር እና በነፃነት መኖር አቅቷቸው ስንቶች በታንኳ ባህርን አቋርጠው፣ እንደ ጨርቅ በኮንቴነር ታሽገው እንዲሁም በረሃን በእግር ጉዞ አቋርጠው የባዕድ አገር ለመግባት እየሞከሩ በየመንገዱ ወድቀው የበረሃ እና የባህር ሲሳይ ሆነው የቀሩትን መመልከት ብቻ በቂ ነው፡፡ እንዚህ ወገኖቻችን የኢኮኖሚው እድገት የፈጠራቸው የሰላም ተጓዥ ወይም ቱሪስት አይደሉም፡፡ እነዚህ ዜጎች የነገ ተስፋቸው የጨለመባቸው የኢኮኖሚ እና የፖለቲካ ግፉዓን ናቸው፡፡

ዛሬ የባዕድ ሃገራትን ያሞቁ ያደመቁት የዚህ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ ስርዓት ግፉዓን አይደሉምን? ታዲያ ምኑ ጋር ነው የምጣኔ ሃብት እድገት ያለው? ዳቦ ቀርቶ ተስፋ መሆን ያልቻለ የኢኮኖሚ እድገት ባለሁለት ሆነ ባለሶስት አሃዝ ምን ዋጋ አለው?

ቢያንስ የተማረውን ወጣት እንኳ የስራ ባለቤት ማድረግ ያልቻለ የኢኮኖሚ እድገት በየትኛውም መለኪያ ተዓማኒ ሊሆን አይችልም፡፡ የአለማችን ግንባር ቀደም ከሚባሉት የኢንቨስትመንት መዳረሻ ከሆኑት ሃገራት ተርታ ‹‹ቀዳሚ ነን›› እያልን የስራ አጥነቱ ከቀን ወደ ቀን በከፋ ሁኔታ እየተባባሰ በቀጠለበት ሃገር ውስጥ የሚኖር ህብረተሰብን ለማሳመን መሞከር እራስን ማሞኘት ነው፡፡

ተምሮ እና ተመርቆ ከቤተሰቡ ጫንቃ ላይ መውረድ የተሳነው ወጣት ባለበት ሃገር ስለ ምጣኔ ሃብት እድገት እና ስለኢንቨስትመንት መስፋፋት መለፈፍ ምንኛ መራር ቀልድ ይሆን?

አርሶ እና አርብቶ አደሩን ከቀዬው እና ከእርሻው ያለምንም አማራጭ በኢንቨስትመንት እና መሰረተ ልማት ስም በማፈናቀል ዘመናዊ የጭሰኛ ስርዓት የፈጠረ የኢኮኖሚ እድገት በየትኛውም ሃገር ታይቶም ተሰምቶም አያውቅም፡፡ በሃገሪቷ አራቱም አቅጣጫዎች ቢኬድ የድህነታቸውን ልክ ለመናገር የሚከብዱ አርሶ አደሮችን እና አርብቶ አደሮችን መመልከት ከባድ አይደለም፡፡ ሞፈር ጨብጠው ስንዴ የዘገኑ እጆች ዛሬ ለስንዴ ልመና ተዘርግተዋል፡፡ ለተጠማኝ ወተት ያጠጡ ሽክናዎች ዛሬ ውሃ አጥተው ተሰቅለዋል፡፡ ላሞች እና ጥጆች ይቦርቁ የነበሩበት የግጦሽ መስክ ዛሬ ተሸንሽኖ ለመንግስት ወዳጆች እጅ መንሻ ውሏል፡፡ ታዲያ ከዚህ በላይ የኢኮኖሚ ድቀት ከወዴት አለ? ታዲያ የግንቦት 20 ትሩፋት የሆነው የተበላሸ የኢኮኖሚ ስርዓት ሰላባ ያልሆነው ማን ይሆን?
ዳር ድንበር ለመጠበቅ ከበረሃ የዋለው ወታደር፣ ዳቦ ራበን ነፃነት እንደውሃ ጠማን የሚሉትን የሚያድነው ታዛዡ ፖሊስና ደህንነት፣ የህዝቦችን ሆድ ለመሙላት ላይ ታች የሚለው አርሶ አደር ወይም አርብቶ አደር፣ የህዝቦች የእውቀት አባት የሆነው መምህር፣ የህዝቦችን ጤና ለመጠበቅ የሚባትለው የጤና ባለሙያ፣ ዘመኑን በትምህርት አሳልፎ ስራ አጥ የሆነው ወጣት… ወዘተ ሁሉም በአንድነት በስቃይ የሚማቅቁበት ሃገራዊ ፍቅራቸው የተሸረሸረበት የተረገመ የኢኮኖሚ ስርዓት እንዴት ማደግ ይቻለዋል?

ትላንትም ዛሬም የዳቦ ጥያቄ መልሱ ጥይት ነው፡፡ ትላንትም ዛሬም የነፃነት እና የዲሞክራሲ ጥያቄ መልሱ እስር እና ግድያ ነው፡፡ ምንም ለውጥ የለም፡፡ ታዲያ የአስተሳሰብ ለውጥ ሳይኖር የኢኮኖሚ ለውጥን እንዴት ማሰብ ይቻል ይሆን?

በመጨረሻም ድህነት የቁጥር ሳይሆን የተግባር መፍትሔ ያሻል፡፡ ማንነታችን ይመስል ድህነት ለረጅም ጊዜ አብሮን ቢኖርም ብቸኛው መፍትሔ ድህንቱን ከቤተመንግስቱ በላይ ጥበቃ የሚያቆምለትን ስረዓት ማስወገድ ነው፡፡ ድህነት በሁለት መንገድ ማስወገድ ይቻላል፡፡ አንደኛው ከደሃው ነጥሎ ድህነትን ማስወገድ ሲሆን ሌላኛው ደግሞ የወያኔ መንግስት በይፋ እየተገበረው ያለው ደሃን ከነድህንቱ በማጥፋት ድህነትን ማጥፋት ነው፡፡ ይህንን መፍትሔ ተግባራዊ የሚያደርጉ ገዚዎቻችን ድህነት ማንነት ነው ብለው ያመኑ ስለሆኑ ነው፡፡


ያላደገ አስተሳሰብ ያደገ ኢኮኖሚ ሊፈጥር አይቻለውም!!!
ቁጥሩ ለተራበ ሰው ዳቦ አይሆን!!!
ስለፍትሃዊ የኢኮኖሚ እድገት ሲባል ይህ ስርዓት-አልባ ስርዓት ይፍረስ!!!
የሳምንት ሰው ይበለን!!! 

Sunday, 15 June 2014

የግንቦት 20 ጫፍ አልባ ቁልቁለቶች




የግንቦት 20 ጫፍ አልባ ቁልቁለቶች-1

መግቢያ
ተጋዳላዮቹሰ ነፍጥ አንግተው ‹‹ብሶት የወለደው የኢህአዴግ ሰራዊት ወታደራዊ ደርግ ሲጠቀምበት የነበረውን የሬዲዮ ጣቢያ ለሰፊው ህዝብ ጥቅም ተቆጣጥሮታል፡፡ ግንቦት 20, 1983›› ብለው አውጀው ሃገሪቷን ከተቆጣጠሩ በኋላ የግንቦት ፀሃይ ቡዳ በልቷቸው ነው መሰለኝ ከአመት አመት እንደ ግንቦት ፀሃይ እያቃጠሉን እንደዋዛ 23 አመታት አልፈዋል፡፡
በግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ስላሴ ጊዜ ከዚህ በታች ድህነት የለም ብለን ነበር፡፡ በዚህ ስርዓት-አልባ ስርዓት ከድህነትም ወጥተን የድህነት አዘቅትም እንዳለ አሳይቶናል፡፡ በወታደራዊ ደርግ ዘመን የጭቆና እና አፈና መጨረሻ አይተናል ብለንም ነበር፡፡ የባሰም አለና ሃገርህን አትልቀቅ እንዳለው ሃገሬ በዲሞን-ክራቱ ኢህአዴግ ዘመነ አገዛዝ ለባርነትም ሆነ ለጭቆና ከእኔ በላይ ላሳር ያለን አገዛዝ ለማየት በቅተናል፡፡
በዚህ ፅሑፍ ስር ደርግ ቁ-1 በሚገባ ተጠናቆ ደርግ ቁ-2 ልዩ ስሙ ኢህአዴግ ስራ ላይ ከዋለ ጀምሮ ባለፉት 23 አመታት ውስጥ ሃገሪቷ እንደ ናዳ ቁልቁል የተንከባለለችባቸውን እንዳንድ ዘርፎች እያነሳን ለማየት እንሞክራለን፡፡ ከእነዚህም ዋነኞቹ የዘር ፖለቲካ አቀንቃኞች መፈልፈያ ማዕከል የሆኑት የትምህርት ተቋማት፣ እንደሸንበቆ እያደገ ነው የተባለለትና የህዝቦችን የመኖር ህልውና እንደሙቀጫ ቁልቁል ያንከባለለው የኢኮኖሚ ስርዓት፣ የባለስልጣናት መፈንጫ የሆነው ፍትሕ አልባ የፍትህ ስርዓት፣ በባለስልጣናት የበላይነት የሚመራውን የህግ የበላይነት፣ ከሃገሪቷ ከ80% በላይ ህዝብን ያሳተፈውና እራሱን እንኳ መመገብ ያልቻለው የግብርናው ስርዓት እና የመሳሰሉትን በዚህ አምድ ስር በተከታታይ በሚወጡ ፅሑፎች ለመዳሰስ እንሞክራለን፡፡

ትምህርት እና ግንቦት 20
ይህ ቁልቁለት እውቅ የዩኒቨርሲቲ ምሁራንን የምን እውቀት እንደሆነ ባልታወቀ ሁኔታ (የጎሳ ተኮር ፖለቲካ እውቀት ሊሆን ይችላል) የ‹‹እውቀት ማነስ›› በሚል ሰንካል (እጅ እግር አልባ) ምክኒያት ከተለያዩ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በተለይም ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ በማባረር ተጀምሯል፡፡
ሃገር ከፍተኛ ወጪ አውጥታ ያስተማረቻቸውን ጉምቱ ምሁራንን ከትምህርት ገበታቸው ላይ በማባረር ከሳይንሱ በላይ ዘረኝነትን በሚሰብኩ የጎጥ ፖለቲካ አቀንቃኝ ምሁራን በመተካት (የመተካካቱ መጀመሪያ ሊሆን ይችላል) የጀመረው ቁልቁለት ሀገሪቷ ዳግም ልታንሰራራ በማትችልበት የትምህርት ጥራት ችግር ውስጥ ከቷት መገኛውን ኮብልስቶን ስር ካደረገው ምሁር ላይ በማድረግ እነሆ 23 አመቱን ሻማ በማብራት እያከበረ ነው፡፡
የትምህርት ጥራት የአንድን ሃገር መፃኢ እጣ ፈንታ ለመተንበይ ከሚያስችሉ መንገዶች ዋነኛው ነው፡፡ የወያኔ መንግስት ስልጣኑን ከተቆናጠጠ በኋላ ሃገሪቷ በትምህርቱ ዘርፍ ትኩረቷን ከጥራት ወደ ብዛት በማሸጋገር (የትራንስፎረሜሽኑ መጀመሪያ ሊሆን ይችላል) ትውልድ አምካኝ የትምህርት ፖሊሲ እየተገበረ ይገኛል፡፡
በአሁኑ ሰዓት በሃገሪቷ ውስጥ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው የትምህርት ፖሊሲ ጥራት ተኮር ባለመሆኑ በዚህ ፖሊሲ ተወዳዳሪ የሆኑ ሙያተኞችን መፍጠር አልተቻለም፡፡ በቂ እውቀት የሌለው ወጣት ማምረት ደግሞ ስርዓቱን የሚሞግት ትውልድ እንዳይፈጠር በማድረግ የስርዓቱን ቀጣይነት በማረጋገጡ ላይ ከፍተኛውን አስተዋፅኦ አድርጓል፡፡ ጥራታቸውን የጠበቁ የትምህርት ተቋማትን ማጥፋት እና ማኮላሸት ዋነኛ እና ቀዳሚ የወያኔዎቹ ስራ የሆነበትም ዋነኛው ምክኒያት ያለፉት መንግስታት የነበራቸው ጥራቱን የጠበቀ እና ነፃ የትምህርት ፖሊሲ በተደጋጋሚ የሚሞግታቸውን ትውልድ በመፍጠር ስልጣናቸውን እንዲያጡ ያደረገው የህዝባዊ ማዕበሉ መነሻ ሆነው ያገለገሉት እነዚህ የትምህርት ተቋማት ናቸው፡፡ የትምህርት ተቋማት የለውጥ ሃዋሪያዎች መፍለቂያ ማዕከላት በመሆን ለዘመናት ሃገሪቷን ማገልገላቸው የነፍጠኞቹ ወያኔዎች ማነጣጠሪያ እንዲሆኑ አስችሏቸዋል፡፡ እነርሱም ለውጡን የዶለቱት እነዚሁ ማዕከላት ውስጥ መሆኑንም መርሳት አያስፈልግም፡፡
ነፍጠኞቹ (ነፍጥ አንጋቾቹ)፣ ጎሰኞቹ እና ጎጠኞቹ የቀየሱት የትምህርት ፖሊሲ በሚገባ ተግባራዊ በመደረጉ ሲጠሩት አቤት ሲልኩት ወዴት ባይ፣ ምክኒያት አልባ፣ መብት እና ክብሩን የሚለምን ትውልድ እንዲፈጠር አድርጓል፡፡ በየከፍተኛ የትምህርት ተቋማቱ የሚገኙ ወጣቶችም በሃገራዊ አንድነት ላይ ከመወያየት ይልቅ አምባገነኑ መንግስት ባቀረበላቸው የጎሰኝነት ድንጋይ መወራወርን ቀዳሚ ተግባራቸው ካደረጉ ሰንበትበት ብለዋል፡፡
ይህንን ስርዓት-አልባ ስርዓት ለማስወገድ በሃገር ውስጥም ሆነ ከሃገር ውጪ ተደራጅተው የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ድርጅቶች በትምህርት ፖሊሲዎቻቸው ላይ ትኩረት ሰጥተው መስራት ተገቢ እና ቀዳሚ ተግባራቸው መሆን ይኖርበታል፡፡ የትምህርት ፖሊሲ ማለት ትውልድ የሚቀረፅበት እንዲሁም የሃገር የወደፊት እጣፈንታ የሚወሰንበት ፖሊሲ በመሆኑ የሁሉም ፖሊሲዎች የጀርባ አጥንት ማለት ይቻላል፡፡
የአንድ ስርዓት ዲሞክራሲያዊነት ማሳያ የትምህርት ስርዓቱ ከፖለቲካ ስርዓቱ ያለው ነፃነት ነው፡፡ የትምህርት ስርዓቱ የፖለቲካ ስርዓቱ አቀንቃኝ ከሆነ ወይም የፖለቲካ ስርዓቱ በከፈተለት ቦይ ብቻ የሚፈስ ከሆነ በሃገሪቷ ያለውን የትምህርት ስርዓት ብልሹነት ማሳያ ነው፡፡ 
በየትምህርት ተቋማቱ በማስተማር እና በመማር ላይ የሚገኙ ምሁራን እና ተማሪዎች ያለምንም ገደብ እና ፍራቻ ሃሳባቸው በነፃነት የመግለጽ መብታቸው ሊከበር ይገባል፡፡ መምህራን እና ተማሪዎች በፍርሃት እየማቀቁ የሚያስተምሩበት እና የሚማሩበት ይህ የአገዛዝ ስርዓት ሊያበቃ ይገባል፡፡
የትምህርት ስርዓቱ ከፖለቲካው ስርዓት ነፃ ባለመሆኑ መምህራን እንደ ገቢ ምንጭ ብቻ የሚጠቀሙበትን ስራ ላለማጣት ተማሪዎችን ከነባራዊ ሁኔታ ጋር እያገናዘቡ ማስተማር ህልም ይሆንባቸዋል፡፡ የመምህራንን ፍራቻ ለማሳየት ተማሪዎቻቸው የሚጠይቋቸውን ጥያቄ ‹‹ይህ ፖለቲካ ነው እንለፈው›› እያሉ እውቀታቸውን ብቻ ሳይሆን ፍርሃታቸውን ወደ ተማሪው የሚያስተላልፉ መምህራን መሰብሰቢያ ማዕከላት ወደ ሆኑት ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት መመልከት ብቻ በቂ ነው፡፡
በግብርና፣ በኢኮኖሚ፣ በሳይንስ እና ቴክኖሎጂ፣ በጤና … ዘርፍ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ላይ በማስተማር የሚገኙ መምህራን የሃገሪቷን ፖሊሲዎች ከነባራዊ ሁኔታ ጋር እያመሳከሩ የመንግስትን ፖሊሲዎች የመተቸት እና አማራጭ የመፍትሔ ሃሳቦችን በማቅረብ መንግስትን ከተሳሳተ ጎዳና የማረቅ ሃገራዊ ሃላፊነት አለባቸው፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ይህንን ትልቅ ሃላፊነት ከመወጣት ይልቅ ስራቸው ላለማጣት እራሳቸውን በፍርሃት አዘቅት ውስጥ ከተው የሚዳክሩ መምህራን መመልከት የእለት ተለት ተግባራችን ከሆነ ውሎ አድሯል፡፡ እነዚህን በፍርሃት ባህር ውስጥ የሚዳክሩ ምሁራንን ከተከናነቡት የፍርሃት ካባ ማላቀቅ ከተቻለ ታላቅ ለውጥ ሃዋርያ ማድረግ ይቻላል፡፡
ሌላኛው የትምህርት ሴክተሩ ቁልቁለት በየትምህርት ተቋሙ የሚቀጠሩ መምህራን በሚቀጠሩበት የሙያ ዘርፍ ካላቸው ችሎታ ይልቅ ያላቸውን የጎሳ ፖለቲካ እውቀት በተለይም ለአገዛዝ ስርዓቱ ያላቸውን ታማኝነት ከግምት ውስጥ ያስገባ በመሆኑ የትምህርት ጥራቱን ቁልቁል በእንብርክክ እንዲሄድ አስገድዶታል፡፡ እነዚህ መምህራን ተብዬዎች ከስርዓቱ ደሞዝ ብቻ ሳይሆን የሚሰፈርላቸው የሚያስተምሩት ወይም የሚያስተላልፉትም እውቀትም ይሰፈርላቸዋል፡፡ እንደገደል ማሚቱ የተባሉትን እና እንዲሉ የተፈቀደላቸውን ብቻ ለተማሪዎቻቸው ያስተጋባሉ ወይም ያስተላልፋሉ፡፡
በመጨረሻም በሃገሪቷ ውስጥ ያሉትን ዘርፈ ብዙ ችግሮች በማያዳግም ሁኔታ መፍትሔ ለመስጠት በሃገሪቷ ውስጥ የሚገኙ የትምህርት ተቋማት ችግር ፈቺ ዜጎችን የማፍራት ተግባራቸው ላይ ያለምንምና ማንም ጣልቃ ገብነት ማተኮር ተገቢ ነው፡፡ የትምህርት ዘርፉ በእውቀት እና በእውነት እንጂ በፖለቲካ ብቃት እና ታማኝነት የሚመራበትን ስርዓት ማስወገድ ቀዳሚ ተግባር ሊሆን ይገባል፡፡ ይህ እስካሆነ ድረስ የትምህርት ዘርፉ የሚያመርታቸው ዜጎች ችግር ፈቺ ሳይሆኑ ችግር ፈጣሪ መሆናቸው አይቀርም፡፡  
ስለትምህርት ጥራት ሲባል ይህ ስርዓት አልባ ስርዓት ይፍረስ!!
የሳምንት ሰው ይበለን!!

Wednesday, 11 June 2014

የእሳት ልጅ ጤዛ



የእሳት ልጅ ጤዛ
መቅደላ ይሉት ፅላት ላይ
ኢትዮጲያ ይሏት ስውር እጅ
በእሳት ልሳን ስትከትብ ሰታኖር የማይጠፋ ቃል
የነብይ እንቦቀቅላ እጆቹን ሽቅብ ዘርግቶ
የታሪክ እውነት ይሞቃል፡፡
እናቱ አገር ልታርቅ
የሞቀ እልፍኟን ጣጥላ ነብዩን በፍቅር አንቃ
እድሜዋን ስትንከራተት
ቀርታለች ካውላላው ሜዳ ወድቃለች ዳግም ላትነቃ
እማማ ደርባባ እመቤት የፍቅር ማማ ብርሃን ….
የፍቅር ፅንስ ራብተኛ የእረፍት ስይታም መሃን
‹‹
ይቅርብኝ የንጉስ ማእድ ውዴን የበላ ጅብ ይብላኝ
ጣረሞት ካሳን ቢጠራ ሳይነጥል እኔንም ይጥራኝ!››
በሰው በፈጣሪ ፊት የቃል ኪዳኗን አክብራ
ተዋቡ መንገድ ቀርታለች አንባው ጫፍ ላይ በውብ ፀዳል በናትነት ሳታበራ !
ባይኖቿ ካሳን እያየች
‹‹
ከሞት አድነኝ አኑረኝ ››
ስትለው በሃዘን ሲቃ!
ስለፍቅር ወንድነት ነጥፎ
ነፍሱ ከውዱ ነፍስ እኩል
በፍቅር ምጡ ተጨንቃ
እነዛ ትንታግ እጆቹ እየተንቀጠቀጡ
አይኖቹ መድህን ፍለጋ ከምድር ሰማይ ሲናጡ
ከእውነት ቁንጮ ሳትደርስ በክናዱ ላይ እንዳለች
ያች የፍቅር ፀዳል ተዋቡ መንገድ ቀርታለች!
ያች የፀደይ ፀሃይ ተዋቡ በጧት ጠልቃለች!
መቅደላ ይሉት ፅላት ላይ
ኢትዮጲያ ይሏት ስውር እጅ
በእሳት ልሳን ስትከትብ ስታኖር የማይጠፋ ቃል
የነብይ እንቦቀቅላ
እጆቹን ሽቅብ ዘርግቶ
የታሪክ እውነት ይሞቃል
ይሄ ከርታታ አባቱ
በቀኙ እጁ የመዳፍ ጥርስ ሽጉጡን እንደነከሰ
በግራው የልጁን እራስ በፍቅር እየዳበሰ
‹‹
አለሜ ራበህ እንዴ ›› ይለዋል በፍቅር ቃሉ
ከአባትና ልጅ ማዶ
በእንግሊዝ የመድፍ አረር እልፍ ጦቢያኖች ያልቃሉ
የእውነት ልጆች ስለሃቅ ከአንባው ስር ይዋደቃሉ
ገብርየ ቁልቁል ሲጋልብ የልብሱ ቀለም ከሩቁ ስንብት ይፈነጥቃል
የእሳት ጅራፍ ከፊቱ ሞት ሊድር ይፈነድቃል
ንጉሱ የቀረውን ሃቅ አንድ ነፍሱን ሊሰዋላት
ከአንባው ጫፍ ሽጉጥ ጨብጦ አገሩን አሻግሮ ሲያያት
እንደኩሩ ወይዘሮ ምድሯ ለምለም ቀሚስ ለብሶ
ለባእድ ያጎበድዳል ወኔዋ በፍራት ፈሶ
‹‹
ምን ዋጋ አለው መልክ ቢያምር ቢሽቆጠቆጥ ልምላሜ
ምድሯ የእውነቷ መንበር መንፈሷ ካልሆነኝ ደሜ ››
የሚል የውስጥ ዋይታው ከአንባው እያስተጋባ
በዝምታው ጥልቅ ባህር ለትውልድ መተላለፊያ የሃቅ ድልድይ ሲገነባ
አለማየሁን ከኋላው አገሩን ከፊት አድርጎ
አይጠላት የልጁ ምድር አይወዳት የጠላት ድርጎ
ግራ ገብቶት እንደቆመ የመድፍ አረር እያፏጨ
ቁልቁል ይወነጨፋል ያለቱን ጥግ እየገጨ
በሞትና እውነት መሃል ስንዝር ሲቀር ውድቀት ሊባጅ
የቴውድሮስ እጅ ቃታ ሲያጠብቅ ለታሪክ ሊነግር አዋጅ
‹‹
አባባ›› ይላል ከኋላው የነብዩ እንቦቀቅላ
በእሳት መሃል የበቀለ የጀግናው ቴውድሮስ መሃላ!
መቅደላ ይሉት ፅላት ላይ
ኢትዮጲያ ይሏት ስውር እጅ
በእሳት ስትከትብ ቃል
የነብይ እንቦቀቅላ
እጆቹን ሽቅብ ዘርግቶ
የታሪክ እውነት ይሞቃል
እንቦቀቅላው ሲባንን መቅደላን ባእድ ረግጧታል
ምድሯ በታሪክ ቁሸት እንደቁሪሳ ጠንብቷል
ነበር ያሉት እውነት ሁሉ ከእውነት አንባ ቁልቁል ሸሽቷል!
ድፍን ጦቢያ እንደማድ ቤት ጥጋ ጥጓ በጥቁር ቀን በመደፈር ጭሽ ጠልሽቷል
ከአንባው ጫፍ ከእውነት ጥግ . . . ብቸኛው እንቦቀቅላ
ከትንታግ አባቱ ሬሳ ተደፍቶ እያለቀሰ
የጦቢያን ቀንዲል ጉልላት ደም ያጨቀየው ሽሩባ በሃዘን እየዳበሰ
የመቅደላን አምባ ጥሶ የመደፈር ዲቃላ ቃል ልኡል አጠገብ ደረሰ!
በባእድ መዳፍ ጉተታ ሽቅብ ተስቦ ሲነሳ
የጨቅላ እጁ ሙጥኝ ብሎ ካባቱ ትኩስ ሬሳ
ደም ያጨቀየው ሹርባ ከደም ጋር የተገመደ
ህብረትን አደራ እያለው ህፃኑ ቁልቁል ወረደ
የተሰበረ ልጅ ቅስሙ በደራሽ ጎርፍ ውስጡ ሟሙቶ
የሳት ልጅ ጤዛ ሆነና ተነነ የሰው ቀን ነግቶ
የቀን ቅንነት ሲጎድል ተወልዶ እውነት ከሸሸ
የምቦቀቅላው ማለዳ ሳያረፍድ ንጋት ላይ መሸ!!

Alex Abreha