Saturday, 22 March 2014

ኢትዮጵያዊነት



አትዮጵያዊነት ለእኔ በቀለበት ይመሰላል፡፡ ቀለበት ፈርጥ ካለው ያምራል፡፡ ያለ ፈርጥ ግን ቀለበት አለ፡፡ ግን አያምርም፡፡ ስለዚህ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ጎሳዎች የቀለበት ፈርጥ እንጂ ቀለበት አይደሉም፡፡ ህልውናቸው ከቀለበቱ ጋር በጥብቅ የተሳሰረ ነው፡፡ ቀለበት ከሌለ ፈርጥ የለም፡፡ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትግሬ፣ ወላይታ፣ ጋምቤላ፣ ጉሙዝ እና ሌሎችም እያልን በሃገሪቷ ውስጥ ያሉትን ጎሳዎች በጠቅላላው ብንዘረዝር የሃገሪቷ ውበቶች ወይም ፈርጦች ናቸው፡፡
woyanne's dream
እያንዳንዱ ጎሳ እና የጎሳ አባል ማወቅ የሚገባው ዋና ነገር ጎሳው ኢትዮጵያዊ በመሆኑ ያገኘው ገፀ-በረከት እንጂ መርጦ እና ፈቅዶ ያገኘው አለመሆኑን ነው፡፡ እኔ ኦሮሞነቴን ወይም አማራነቴን ያገኘሁት ኢትዮጵያዊ በመሆኔ ነው ብሎ ማሰብም ሆነ ማመን ያስፈልጋል፡፡ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ እኔ ኢትዮጵያዊ ባልሆንም ኦሮሞ፣ አማራ ወይም ትግሬ ወይም ሌላ ጎሳ መሆን እችላለሁ የሚል ግንዛቤ እውነትነት የሌለው የትም የማያደርስ መንገድ ነው፡፡ አንዳንድ ያወቅን የነቃን የጎሳ አባላት ነን የሚሉ ‹‹አላዋቂ አዋቂዎች ወይም አለማወቃቸውን የማያውቁ አዋቂዎች›› ማንነታቸውን እና መሰረታቸውን ረስተው የሚያራምዱት መርዘኛ አስተሳሰብ የትም አያደርስም፡፡
እንዴት እና በየትኛው መመዘኛ አሮሞ ኢትዮጵያዊ ከመሆኑ በፊት አሮሞ ሊሆን እንደሚችል ‹‹የኦሮሞ ፈርስት›› አስተሳሰብ ጠንሳሾች እና አራማጆች ማስረዳት የሚያስችል የእውቀትም ሆነ የሞራል ብቃት ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ኢትዮጵያዊነት እራሳቸው በየጓዳው የሚያበስሉትን መርዝ እንደማስረጃነት ለማቅረብ ሊያስገቡበት የሚችሉበት ምንም ክፍተት የለውም፡፡ ሊጠቀሙበት የሚችሉት ብቸኛው ክፍተት የወያኔ መንግስት ያዘጋጀላቸውን የጎሳ ፖለቲካ ብቻ ነው፡፡ 
እኔ አሮሞነቴ በኢትዮጵያዊነቴ ያገኘሁት ሽልማት እንጂ አውሮፓ ወይም አሜሪካ ወይም ኢሲያ ወይም የተቀረው አፍሪካ ውስጥ ብወለድ አሮሞነትን የሚያክል ትልቅ ገፀ-በረከት አገኛለሁ ብሎ ማሰብ የቁም ቅዠት ብቻ ሳይሆን እብደትም ነው፡፡ ምናልባት ‹‹የኦሮሞ ፈርስት›› አስተሳሰብ ጠንሳሾች እና አራማጆች በዚህ ሰዓት እኔን ለመሞገት የሚጠቀሙበት ክፍተት ቢኖር በኬኒያ፣ በሩዋንዳ፣ በዩጋንዳ፣ …ያለው ኦሮሞ ኦሮሞነቱን እንዴት አገኘው ብለው ሊሆን ይችላል፡፡ ለዚህ ቀለም እና ወረቀት ከማባከናቸው በፊት መልሼ ማለፍ ይኖርብኛል፡፡
በተጠቀሱት አገሮች የሚገኘው ኦሮሞ ‹‹የኦሮሞ ፈርስት›› አስተሳሰብ ጠንሳሾች እና አራማጆች በስደት በአውሮፓ እና አሜሪካ እንደሚኖሩት ሁላ በኢትዮጵያዊነቱ የኦሮሞነት ገፀ-በረከቱን ከተረከበ በኋላ በተለያዩ ገፊ ምክኒያቶች (pushing factors) ሃገሩን ጥሎ በመሰደድ አሁን ባለበት አጎራባች አገሮች ለመኖር የተገደደ ነው፡፡ እዚህ ጋር መርሳት ያልነበረባቸው ጉዳይ እነርሱ ዛሬ አሜሪካ ወይም አውሮፓ ሆነው የሚያቀነቅኑት የጎሳ ተኮር ፖለቲካ መነሻቸው እዚሁ ኢትዮጵያ መሆኑን ነው፡፡ ለምን አውሮፓዊ፣ አሜሪካዊ፣ … የሆነ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትግሬ፣ ወላይታ፣ ከምባታ፣ …ሊኖር አልቻለም፡፡ የእነዚህ ሃገሮች ማሕፀን እነዚህን ጎሳዎች ለመፍጠር  ስላልተመረጠ ወይም የሚያስችል አቅም እና ብቃት ስለሌለው ነው፡፡
እነዚህ ‹‹የኦሮሞ ፈርስት›› አስተሳሰብ ጠንሳሾች እና አራማጆች የሚያራግቡት የአባቶቻቸውን ታሪክ ሳይሆን የአባቶቻቸውን ጠላቶች ታሪክ ነው፡፡ እንደ ኢህአዴግ የኦሮሞን፣ የአማራን፣ ወይም የትግሬን ህዝብ የበደለ ከየትም ሊመጣ አይችልም፡፡  እውነት እነዚህ ሰዎች እንደሚሉት አባቶቻቸው በኢትዮጵያዊነታቸው ላይ እምነት የላቸውም? የኦሮሞ ህዝብ አድዋ ዘምቶ በኢትዮጵያዊነቱ የመጣበትን ጠላት መግቢያ መውጫ አላሳጣም?
ለነገሩ እነዚህ ሰዎች ጎበናን የሚያክል ጀግና እንዲሁም ባልቻን የሚያክል የጦር ገበሬ ኦሮሞነት ሲክዱ ማንነታቸውን ወይም አሮሞነታቸውን ክደዋል፡፡ እነዚህ ከላይ የጠቀስናቸው ሃገራችን በታሪኳ ዳግም ልታፈራቸው ያልቻለች ጀግኖች ለኢትዮጵያዊነት ክብር ደማቸውን አፍሰው፣ አጥንታቸውን ከስክሰው እንዲሁም ውድ ህይወታቸውን ያለማወላወል ገብረዋል፡፡ የኢትዮጵያዊነት ክብር ሳይኖር የኦሮሞነት  ክብር ሊኖር እንደማችል ቀድሞውኑ ተረድተው ነበር፡፡ አሮሞነት ያለ ኢትዮጵያዊነት ምንም አቋራጭ መንገድ እንደሌለ አበክረው አምነው ነበር፡፡ ‹‹ጅራቷ ያደርሳል ካናቷ›› እንደሚባለው ታዲያ እነዚህ ሰዎች የሚያወሩት እና የሚያቀነቅኑት ኦሮሞነት የአባት የቅድመ-አያታቸውን ወይስ የኢትዮጵያ እና የኢትዮጵያዊነት ጠላት በሆነው የወያኔ መንግስት ለአገዛዝ እንዲያመቸው ያቀበላቸውን አሮሞነት?
እኔ ይህንን ፅሁፍ ስፅፍ ባልቻ እና ጎበና የሞቱለትን በኢትዮጵያዊነቴ ያገኘሁትን ኦሮሞነት መሰረት አድርጌ ነው፡፡ ለእኔ ባልቻ ኦሮሞ ነው፡፡ ለእኔ ጎበና ኦሮሞ ነው፡፡ ለእኔ የእነዚህን ጀግኖች ኦሮሞነት ክዶ አሮሞነት ሊኖር አይችልም፡፡ አንዳንዶች መለስ እና ግብራበሮቹ (አጫፋሪዎቹ) ካደረሱብን በደል ተነስተው ኢትዮጵያዊነታቸውን ጥያቄ ውስጥ ሲያስገቡ የባሰባቸውም ኢትዮጵያዊነታቸውን ሲገፉ መመልከት የተለመደ ነው፡፡ የወያኔዎች ኢትዮጵያዊነት መካድ የራስን ኢትዮጵያዊነት መካድ ነው፡፡ የእነዚህን ሰዎች ኢትዮጵያዊነት ይቅረብም ይራቅ ከእኛ ኢትዮጵያዊነት ጋር የተጋመደ ነው፡፡ የአንዱን ኢትዮጵያዊነት ለመግፈፍ ስንሞክር የራሳችንን እንዳንገፍ መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡
ኢትዮጵያዊነትን ማንም ሰው ሲያሰኘው የሚሾመው የሚሸልመው ሲያሰኘው ደግሞ የሚገፈው ማዕረግ አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች ከሰው ተፈጥረው ሰው ለማጥፋት ታትረው የሚሰሩ እንዳሉ ሁሉ ከኢትዮጵያ ማሕፀን ተፈጥረው አትዮጵያ፣ ኢትዮጵያዊያን እና ኢትዮጵያዊነት ለማጥፋት ቀን ከሌት ተግተው የሚሰሩ የአስተሳሰብ እና አመለካከት ስህተት ያላቸው ኢትዮጵያዊያን ናቸው፡፡ ይህ ስህተት ማረም የሚቻለው ኢትዮያዊነትን በመግፈፍ ሳይሆን አመለካከት እና አስተሳሰባቸውን በተሻለ አመለካከት እና አስተሳሰብ ለመተካት ታትሮ በመስራት ነው፡፡
የጎበናንም ሆነ የባልቻን ኦሮሞነት የመግፈፍ ወይም ጥያቄ ውስጥ የማስገባት የሞራል ብቃት ሆነ መብት ያለው አንድም ግለሰብ የለም፡፡ ምናልባት እነዚህ ሰዎች ኢትዮጵያዊነታቸው ከኦሮሞነታቸው በልጦባቸው ጥቂቶችን በማወቅም ሆነ ባለማወቅ ‹‹ያስቀየመ›› ተግባር ፈጽመው እንኳ ቢሆን ኦሮሞነትን ሊያስገፍፍ የሚችል አንዳችም ተግባር የለም፡፡
የኦሮሞ ህዝብ እንደተቀሩት ህዝቦች እና ጎሳዎች በኢትዮጵያዊነቱ ያገኘው እንጂ ያጣው አንዳችም ነገር የለም፡፡ ነገር ግን በተለያዩ ወቅቶች በሃገሪቷ ስልጣን ላይ በወጡ ገዢዎች የኦሮሞን ህዝብ እንደተቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ ሁሉ ሲጨቆን መኖሩ የማይካድ ሃቅ ነው፡፡ ይህንን የኦሮሞ ህዝብ በኦሮሞነቱ የተቃጣበት ችግር ብቻ ሳይሆን በኢትዮጵያዊነቱ የተቃጣበት ችግር ነው፡፡ የኦሮሞን ህዝብ ከተቃጣበት ችግር ለማላቀቅ ብቸኛ መፍትሔው የኢትዮጵያን ህዝብ ከባርነት እና ጭቆና ነፃ ማውጣት ብቻ እና ብቻ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃ ወጥቶ የኦሮሞ ህዝብ በባርነት የሚኖርበት ሁኔታ እና ምክኒያት የለም፡፡ መላው የኢትዮጵያ ገሳዎች ከኢትዮጵያዊነታቸው በሚያገኙት ትሩፋት ልክ የኦሮሞ ህዝብም ተጠቃሚ ይሆናል፡፡
ማንኛውም ጎሳ አማራም ሆነ ትግሬ በኢትዮጵያዊነት ውስጥ ያላቸው ድርሻ ከየትኛውም ጎሳ አይበልጥም፤ አያንስምም፡፡ ሁሉም ጎሳዎች በኢትዮጵያ ውስጥ ያላቸው የባለቤትነት ድርሻ እኩል ነው፡፡ ማንኛውም ጎሳ ይህንን አምኖ ከተቀበለ በኢትዮጵያዊነት ላይ ምንም ጥያቄ ሊያነሳ አይችልም፡፡
የኦሮምን ህዝብ ኢትዮጵያዊነት የሚጠራጠሩ ግለሰቦች እና ስብስቦች ለኦሮሞ ህዝብ ጥፋትን እንጂ ልማትን የሰነቁ አይደሉም፡፡ የኦሮሞን ህዝብ አትዮጵያዊነትን መካድ ለኢትዮጵያዊነት የተዋደቁ የኦሮሞ ጀግኖችን መካድ ማለት ነው፡፡ የኦሮሞ ህዝብ ኢትዮጵያዊ ባይሆን ኖሮ አድዋ ድረስ ዘምቶ ባልደማ ወይም ባልሞተ ነበር፡፡ የኦሮሞ ህዝብ አድዋ ድረስ የዘመተው ተገዶ ወይስ አድዋ የኦሮሞ ግዛት ነው ብሎ? በእኔ አመለካከት ለሁለቱም መልሱ አሉታዊ ነው፡፡ ማለትም የኦሮሞ ህዝብ አድዋ ድረስ ሂዶ የደማውም ሆነ የሞተው ተገዶ ወይም ግዛቱ ስለሆነ ሳይሆን በኢትዮጵያ ላይ የተቃጣውን አደጋ የመጋፈጥ እና የመቀልበስ ኃላፊነት እና ግዴታ እንዳለበት አምኖ ስለተቀበለ ነው፡፡
በመጨረሻም እኔ ኦሮሞነቴን በኢትዮጵያዊነቴ ያገኘሁት ነው፡፡ ከኢትዮጵያዊነት የተለየ ኦሮሞነትም የለኝም፡፡ ሊኖረኝም አይችልም፡፡ ስለዚህ መጀመሪያ ኢትዮጵያዊ ነበርኩ፡፡ ኩሩ ኢትዮጵዊ በመሆኔ ኢትዮጵያ ሃገሬ አሮሞ የሚባል ጎሳ በገፀ-በረከትነት አበረከተችልኝ፡፡ እኔም ይገባኛል ብዬ ተቀበልኳት፡፡ ለሌላው ወንድሜ አማራ፣ ለሌላዋ እህቴ ትግሬ፣ ሌላዋ ወላይታ፣ ለሌሎቹ ደግሞ ሌላ ተበረከተላቸው፡፡ ወደው አክብረው ተቀበሉት፡፡  እኔ ኦሮሞነቴን በማከብረው እና በምወደው ልክ ሌሎች ጎሳዎችን እወዳለሁ፤ አከብራለሁ፡፡ ከእነርሱም የተለየ ማንነት የለኝም፤ ሊኖረኝም አይችልም፡፡ 
እዚህ ጋር ኢትዮጵያን እና ኢትዮጵያዊነትን በጀውራራ አይን ለሚያዩት ለጅዋር እና ለጅዋራዊያን መልክቴን ላስተላልፍ… ኦሮሞ ለመሆን ብቸኛው መንገድ ኢትዮጵያዊ መሆን ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነትን አዋርዶ ኦሮሞነትን ማስከበር አይቻልም፡፡ ኢትዮጵያዊ ለመሆን ብቸኛው መንገድ አፍሪካዊ መሆን ነው፡፡ አፍሪካዊ ሳይሆኑ ኢትዮጵያዊ መሆን አይታሰብም፡፡ ኢትዮጵያዊ ሳይሆኑ ኦሮሞነት የለም!!!
ስለዚህ ‹‹ቦይ-ኮት›› ብለህ በነካው እጅህ የአባትህን ታሪክ ባቆሸሸው ወያኔ ላይ ‹‹ቦይ-ኮት ወያኔ›› አውጁበት፡፡ ያለ እዚህ መንግሰት አትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊ ክቡር ነው፡፡ ይህም ማለት የኦሮሞ፣ የአማራ፣ የትግሬ፣ …ህዝብ ክቡር ነው፡፡   
ክብር ለኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያዊያን ይሁን!!
የነገ ሰው በለን!!                

የሰማያዊ ትውስታዬ



ሰሞኑን በግል ጉዳይ ምክኒያት ከተለያዩ እንቅስቃሴዎች ተቆጥቤ አብዛኛውን ጊዜን ከቤተሰብ እና ከቅርብ ዘመዶቼ ጋር የማሳለፍ ላይ እገኛለሁ፡፡ ከቤተሰቦቼ በተለይም ከእናት እና አባቴ ጋር ስለ ፖለቲካ ሕይወቴ በሰፊው እና በግልፅነት የማውራት እድሉ ገጥሞኛል፡፡ ይህንን ስል ከዚህ በፊት ከቤተሰቦቼ ጋር በዚህ ጉዳይ ላይ አላወራም ነበር ማለት መስሏችሁ የተረዳችሁ ካላችሁ ፈጽሞ ተሳስታችኋል፡፡ ፍፁም ከቤተሰቤ የተደበቀ ህይወት የለኝም፡፡ እያንዳንዷን ነገር ላይ የጥንቃቄ ምክራቸውን አይነፍጉኝም፡፡ እያንዳንዷን እርምጃዬን በጥንቃቄ አደርግ ዘንድ የዘወትር ምክራቸው ነው፡፡ እዚህ ጋር ቤተሰቦቼ እኔ ያለሁበትን የፖለቲካ አመለካከት ከልባቸው ደፍሬ ይደግፋሉ ማለት ባልችልም እኔን የሚያስደስተኝ ነገር ሁሉ እንደሚያስደስታቸው በሚገባ ስለማውቅ አሁን ባለሁበት የፖለቲካ ተሳትፎ ደስተኛ ናቸው ለማለት እደፍራለሁ፡፡
አንድ ቀን ጠዋት እናቴ አዳሬን ለማየት ወደተኛሁበት ክፍል መጣች፡፡ ወደ ክፍሉ ስትገባ እኔ እና አባቴ ክፍሉ ውስጥ ነበርን፡፡ አባቴ የተለመደ ምክሩን እየሰጠኝ ነበር፡፡
‹‹ልጄ›› ብሎ ነበር የጀመረው፡፡ ‹‹ልጄ ስለ እውነት ኖረክ ስለ እውነት ብቻ ሙት፡፡ እኔ ስለ እውነት ብለህ፣ ስለዚች ሃገር ክብር እና ስለህዝቧ ፍቅር ስትል በምታደርገው ትግል ውስጥ ብትታሰር ወይም የአካል ወይም የህይወት መሰዋዕት ብትሆን የኩራት እንባ አነባ እንደሆን እንጂ አንድም ሃዘን አይሰማኝም፡፡ የመረጥከው መንገድ ትክክልም ይሁን አይሁን ሁል ጊዜም ለመረጥከው መንገድ ወይም ለእውነትክ መሰዋዕት ለመሆን ወደኋላ እንዳትል፡፡ ልጄ ጀግንነት ለቆሙለት አላማ አስፈላጊውን መሰዋትነት ለመክፈል ዝግጁ መሆን ብቻ ሳይሆን መክፈልም ጭምር ማለት ነው፡፡ በህይወት ቆይታህ ስለህዝብ ፍቅር፣ ስለሃገር ክብር እና ነፃነት መሞት ከመኖር የተሻለ መኖር ነው፡፡ በሰዎች ልብ ውስጥ ነግሰህ ትኖራለህ፡፡ ነገር ግን የውሸት ኖረክ ስለ ሆድክ አድረክ የሞትክ ቀን ዳግም ሞት ትሞታለህ፡፡ ስለ ውሸት መኖር እና ስለሆድክ ማደር የጀመርክ ቀን በሰዎች ልብ ውስጥ ትሞታለህ፡፡ ልጄ አካላዊ ሞት ከመሞትህ በፊት እንዳትሞት ተጠንቀቅ፡፡ ድሮ ኢህዴጎች ጫካ ሲገቡ የትግሬ እናት ልጇን ምን ብላ እንደመረቀች ታውቃለህ? "ጥይት ጀርባህን እንዳይመታህ" ነበር ያለችው፡፡ ይህንን ስትል ማስተላለፍ የፈለገችው ነገር ለጥይት ግንባርህን ስጥ እንጂ ስትሸሽ ጀርባህ ተመትተህ እንዳትሞት ማለቷ ነበር፡፡ አንተም ዛሬ የምመክርህ ነገር ስለእውነትህ ከሆነ ግንባርህን ሳታጥፍ ግንባርህን ለጥይት ወይም አንገትህን ለገመድ ስጥ›› እያለ ምክሩን ሲለግሰኝ ሁለታችንም የእናቴን ወደ ክፍሉ መግባት አላስተዋልንም ነበር፡፡
‹‹ሁሉም ነገር እውነት ነው›› በማለት ንግግሯን ጀመረች፡፡ ቀጥላም ‹‹ምክርህ ሁሉ መልካም ነው፡፡ ነገር ግን የትግሬዋን እናት ምክር የተረጎማችሁበት መንገድ ትክክል አይመስለኝም፡፡ የልጇን ጀግንነት እና ፈሪነት ከእናት በላይ ማን ያውቃል? የትግሬው ታጋይ እናት ልጇ ፈሪ እንዳልሆነ በሚገባ ታውቅ ነበር፡፡ ጥይት ጀርባህን እንዳይመታህ ስትል አትሽሽ ማለቷ አልነበረም፡፡ ልጇ እንደማይሸሽማ ታውቃለች፡፡ መቼም የጥይት መዓት ወደሚበተንበት ጫካ የሚሄደው ልጇ የደርግ ወታደር ፈንዲሻ እየበተነ ይቀበለኛል ብሎ እንደማያስብ ታውቃለች፡፡ ያቺ እናት ጥይት በሚያውካካበት ግንባር የከበሮ ድምድምታ የሚጠብቅ ልጅ ወልዳ እንዳላሳደገች ታውቃለች፡፡ የትግሬ እናት እንደዚያ ብላ የመረቀችው አብረውክ ጫካ የሚገቡትን ሰዎች ተጠንቀቅ ማለቷ ነው፡፡ ከኋላ በጥይት እንዳትመታ ማለቷ ነበር፡፡ አንተ ሃገር እና ወገን ብለህ ግንባርህን ለጥይት ስትሰጥ ስልጣን እና ሃብት ብሎ ጫካ ከገባ ሰው ጀርባህን ጠብቅ ማለቷ ነበር፡፡ እኔም ዛሬ አንተን የምልህ ስለእውነት ግንባርህን እንደማታጥፍ በሚገባ አውቃለሁ፡፡ እውነትክን ለመከላከል አባትህ እንዳለው ግንባርህ ለጥይት እና አንገትህን ለገመድ እንደምትሰጥ አልጠራጠርም፡፡ ልጄ እውነትህ ሃገርህ ናት፡፡ እውነትህ ወገንህ ነው፡፡ ከእነዚህ ውጪ እውነት የለህም፡፡ በአንተ እና በመሰሎችህ እውነት ተከልለው የውሸትና የጥፋት ተልዕኮ ከሚያራምዱ ሰዎች ጀርባህን ጠብቅ፡፡ ልጄ ለሚያምኑበት ሰው ነው ጀርባ የሚሰጠው…፡፡ በዚህ ወቅት ለመሞት እንጂ ለመግደል ጫካ እንድትገባ እና ከወንድሞችና እህቶችህ ደም እንድትቃባ አልመክርህም፡፡ ልጄ ሃገር በደም አትገነባም፡፡ ሰው ለማኖር ሰው ይሞታል እንጂ ሰው አይገደልም፡፡ በአለም ላይ በመሞቱ እንጂ በመግደሉ ሰው ያኖረ ጀግና የለም፡፡ ሙት እንጂ አትግደል፡፡ እውነተኛ ታጋይ ከሆንክ የትግል አጋሮችህን ስቃይ አንተ ለመሰቃየት እንዲሁም ሞታቸውን ለመሞት እራስህን ቅድሚያ አዘጋጅ፡፡ ጀግና ሰው ለመሰዋዕትነት ይሽቀዳደማል›› ብላ አባቴን አስከትላ ወጣች፡፡
ከዚያ በኋላ የቤተሰቦቼን ምክር አሰላሰልኩት፡፡ በተለይም ‹‹ለሚያምኑበት ሰው ነው ጀርባ የሚሰጠው›› የሚለውን የእናቴን ምክር አሰብኩት፡፡ እውነት ነው፡፡ ግንባርን በአይን ጀርባን በወዳጅ ማስጠበቅ ያስፈልጋል፡፡
ከዚያማ አብረውኝ የምታገላውን የትግል ጓዶቼን አሰብኩ፡፡ በሃሳብ እሁድ ማርች 9/ 2014 መገናኛ አደባባይ የሴት የትግል አጋሮቼን የነፃነት ሩጫ ለመታደም ከወንድ ጓዶች ጋር ታድሜ ነበር፡፡ በመነሻው አከባቢ ስለነበርን ሩጫውን እየተከታተለ መረጃዎችን እንዲያደርስ ከተመደበው ቡድን ጋር በስልክ ሁሉም ነገር መልካም እና ሰላማዊ በሆነ ሁኔታ እየተካሄደ እንዳለ በመስማታችን ሁላችንም ፊት ላይ የደስታ ስሜት ይስተዋል ነበር፡፡ ትንሽ በአከባቢው ዞር ዞር ብለን ሴቶቻችን ሩጫው መጠናቀቂያ አከባቢ እየደረሱ መሆኑን ስለተነገረን ወደ አከባቢው ተመለስን፡፡ ከጥቂት ጉጉት በኋላ ጀግኖቻችን ቦታቸው ላይ ደረሱ፡፡ ሁላችንም እጃችንን በማውለብለብ በሰላም በመምጣታቸው እንዲሁም ሃሳባቸውን በነፃነት በማንጸባረቃቸው ደስታችንን እና ድጋፋችንን ገለጥንላቸው፡፡
ነገር ግን ሴት ጀግኖቻችንን የተቀበላቸው የእኛ እቅፍ ሳይሆን የፖሊስ እጅ ነበር፡፡ ይህ ሊሆን እንደሚችል የገመትነው ነገር ቢሆንም ጀግኖቻችንን አቅፈን ደግፈን ለመቀበል የነበርን ጉጉት በአጭሩ በመቀጨቱ ነው መሰል ሁላችንም ፊት ላይ የነበረው ቁጣ እና ሃዘን ለመግለጽ ይከብድ ነበር፡፡ በዚህ ሰዓት ሁላችንም ከፖሊሶቹ ጋር ብንተናነቅ ደስ ባለን ነበር፡፡ ግን ያንን ማድረግ ከትርፉ ኪሳራው ስለሚያመዝን ሁለቱ ጀግኖች (ብርሃኑ እና ጌታነህ) ፖሊሶቹን ሴቶቹ ለምን እንደተያዙ ለመጠየቅ ተለይተውን ሄዱ፡፡ እኛ ባለንበት ቦታ ሆነን ሁኔታውን በአንክሮ መከታተላችንን ቀጠልን፡፡ ፖሊስ ለቀረበለት ተገቢ ጥያቄ የሰጠው መልስ ወንዶቹን በአባሪ ተባባሪነት ከሴት ጀግኖቻችን ጋር መቀየጥ ነበር፡፡ ከዚያም ከእኛ ጋር የነበረው ጀግናው ወጣት አቤል የሴቶቹን ጀግኖች ስልክ በአንድ ቦርሳ ውስጥ ሰብስቦ ይዞ ስለነበር በፖሊሶች እይታ ስር ወደቀ፡፡ በቁጥጥር ስርም አዋሉት፡፡ በዚህ ወቅት ፊቱ ላይ ይነበብ የነበረው ጀግንነት እና የአላማ ጽናት በቃላት መግለጥ ከምችለው በላይ ነው፡፡
እዚህ ጋር ‹‹እውነተኛ ታጋይ ከሆንክ የትግል አጋሮችህን ስቃይ ቅድሚያ አንተ ለመሰቃየት እንዲሁም ሞታቸውን ቅድሚያ ለመሞት እራስህን አዘጋጅ›› የሚለውን የእናቴን ምክር አስታወሰኝ፡፡ እነዚህ ጀግኖች ስቃዬ ለመሰቃየት እንዲሁም እስራቴን ለመታሰር እራሳቸውን አሳልፈው የሰጡ እውነተኛ ታጋዮች ናቸው፡፡ በዚህ አጋጣሚ የጣይቱ ልጆች ስለሆኑት ሴት ጀግኖች ስናወራ ወንዶችን አናብስት እንዳንረሳ ለማስታወስ እወዳለሁ፡፡ ለመጨረሻ ጊዜ ከእነዚህ አናብስት ጋር የተገናኘነው ከፍርድ ቤት ተመልሰው በእስር ቤት ውስጥ ነበር፡፡ ሳይባቸው የነበረው በራስ መተማመን እና ጀግንነት አንዳችም ሳይቀንስ እንዲያውም ጨምሮ ነበር፡፡ ያ የመጨረሻ አካላዊ ትውስታዬ ነው፡፡ በምናብ ግን ሁሌም አብሬያቸው ነኝ!!
በመጨረሻም፤ እኔ እድለኛ ነኝ፡፡ ስቃዬን ለመሰቃየት፣ እስራቴን ለመታሰር እንዲሁም ሞቴን ለመሞት የተዘጋጁ እውነተኛ ታጋዮች ያሉበት ሰማያዊ ቤት ገብቻለሁ፡፡ አሁንስ ‹‹ጀርባዬን ለማን እሰጣለሁ?›› ብዬ አልጨነቅም፡፡ ከጀርባቸው በላይ ጀርባዬን የሚጠብቁልኝ ጀግና የትግል አጋሮች አሉኝ፡፡ ‹‹ጀርባ ለወዳጅ ነው የሚሰጠው›› ነው ያልሽው እማሚ? እውነት ነው፡፡ ቢያንስ ጀርባዬን መከራ እንደማያገኘው አረጋግጫለሁ፡፡ እውነተኛ የትግል ስልት እና እውነተኛ ታጋዮች ይዤ ለምን እፈራለሁ፡፡ እውነትን ይዤ በሞት ጨለማ ውስጥ እንኳ ብሔድ አልፈራም!! አባቢ እውነትህን ነው ስለእውነት፣ ስለሃገር፣ ስለወገን ነፃነት ግንባሩን ለጥይት እንዲሁም አንገቱን ለገመድ የሚሰጥ ኢትዮጵያዊ አድርገህ አሳደከኝ እንጂ ፈሪ አላደረከኝም፡፡ ክብር እና ምስጋና ለእናንተ ይሁን!!!
ፍቅር፣ ብርታቱን እና አንድነቱን አይንፈገን!!
የነገ ሰው ይበለን!!            

Friday, 21 March 2014

ሞቷል እንቅበረው



የሳው "መንግስት" (መንግስት ብሎ መጥራት ስለሚከብደኝ) በዜጎቻችን ላይ የሚያደርሰውን ግድያ እና እንግልት ለመቃወም የወገን ስቃይ ስቃያችን በደላቸው ደግሞ በደላችን ነው ብለው አደባባይ የወጡ  ላይ የኢህአዴግ "መንግስት"  (መንግስት ብሎ መጥራት ስለማልችል) ከየትኛውም የመንግስት አይነት በማይጠበቅ ሁኔታ የፈፀመው አፀያፊ እና አሳፈሪ ተግባር የምገልጽበት ቃላት በመፈለግ ላይ ባተኮርኩበት ወቅት ነበር አንድ ተረት ትዝ ያለኝ፡፡ ተረቱን አንዲት ጓደኛዬ ከሰጠችኝን  "ኑሮ እና ፖለቲካ" የሚለው የበሃይሉ /እግዚያብሔር መጽሐፍ ላይ ነበር ያነበብኩት፡፡ እንዲህም ይነበባል… ከሁሉ በፊት ግን ለመጽሐፉን ደራሲ ብሎም መጽሐፉን አነበው ዘንድ ለሰጠችኝን ወዳጄን ከመቀመጫዬ ብድግ እንዲሁም ከወገቤ ጎንበስ ብዬ ምስጋናዬ ማቅረብ ይኖርብኛል፡፡
በአንድ ወቅት ከህግ እና ከደንብ እንዲሁም ከሃገራዊ ጥቅም ውጪ በመንቀሳቀስ የግል ጥቅሙን በሚያሳድድ ግለሰብ ላይ ውሳኔ ለማሳለፍ እና እርምጃ ለመውሰድ ምክር ቤቱ ስብሰባ ይዟል፡፡ የክሱ አቅራቢ "ይህ ሰው እኛ ካበጀንለት ስርዓት ውጪ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ህጋችንን ጥሷል፡፡ ከሃገራዊ ጥቅም ይልቅ ለራሱ ጥቅም እየተጋ ስለሆነ ምን እናድርገው? በሉ አንድ ውሳኔ እንስጥና ወደ ጉዳያችን እንመለስ" በማለት ክሱን አቀረበ፡፡
ከወደ ጥግ አንድ እጅ ተመዘዘ፡፡ "ምን እናደርገዋለን? እርሱ ከህዝብ ይበልጣልን? ማስወገድ ነዋ!!" ሲል ቁጣ በተሞላ አንደበት ተናገረ፡፡ ቤቱ ሃሳቡን ተቀበለው፤ "አዎ እንግደለው! እንግደለው!" ሲልም ተንጫጫ፡፡ "ፀጥታ! ፀጥታ!" የምክር ቤቱ ሰብሳቢ ቤቱን ስረዓት ለማስያዝ ሞከሩ፡፡ "አዬ! እንዲህ አይነት መናኛ ሰው እያለ ምን ስርዓት አለ? ምንስ ጸጥታ አለ? መግደል ነው፤ መገላገል!!" በማለት ተሰብሳቢው አጉረመረመ፡፡
"አንድ ጊዜ! እባካችሁአንድ ጊዜ!" ከወደ መሃል አንድ እጅ ተመዘዘ፡፡ ከብዙ ጭቅጭቅ በኋላ በሰብሳቢው ጥረት እና ውሳኔ ተፈቀደለትና "አመሰግናለሁ!" በማለት ንግግሩን ጀመረ ቀጥሎም "ሰውዬውን ለመግደል መወሰናችሁ አልገባኝም!" ህዝቡ ግር ተሰኘ፡፡ "እንዴት!" አሉ ጥቂት የማይባሉ ተሰብሳቢዎች በብስጭት፡፡ ተናጋሪው ረጋ ብሎ "ሰውዬው እኮ አስቀድሞ ሞቷል!" አለ፤ ቀጥሎም "ባይሞት ኖሮ የዚህን ማህበረሰብ ክብር የሚነካ ነውር ይፈጽም ነበርን? ባይሞት ኖሮ የዚህ ህዝብ ሰላም ያደፈርስ ነበር? ስለዚህ እኔ የምለው ይገደል ሳይሆን ይቀበር ነው" ሲል ሃሳቡን ቋጨ፡፡
ተሰብሳቢዎቹ ተደሰቱ፡፡ የሚፈልጉት ይህንን ነበርና፣ "ድንቅ ሃሳብ!" ሲሉ አደነቁ፡፡ "ሞቷል እንቅበረው!!" በሚለው ተስማሙ፡፡ ወድያው ሰውዬው ዘንድ የሚሄድ ኮሚቴ ተቋቋመ፡፡
የኮሚቴ አባላት በፍጥነት ትእዛዙን ለማስፈጸም ወደ ሰውዬው ቤት ሄዱ፡፡ በሩንም አንኳኩ፡፡
"አቤት!" አለ ሰውዬው በቡድን የመጡትን ለማወቅ እየተቸገረ፡፡
"የመጣነው ይዘንህ ለመሄድ ነው፡፡"
"የት?"
"ቀብር!"
"ማን ሞተ?"
"አንተ!"
"አልገባኝም!!" ግራ መጋባቱን ለማሳየት ዓይኑን የኮሚቴው አባላት ላይ አንከራተተ፡፡
"ባንተ ላይ ትልቅ ጉባኤ ተካሂዶ ነበር፡፡ በጉባኤውም ሞቷልና ቅበሩት ተብሎ ውሳኔ ተወስኖብሃል፡፡"

ሰውዬው ደነገጠ፤ "ይህ የቂል ውሳኔ ነው! እኔ አልሞትኩም፡፡ እንደ እናንተ እያወራሁ፣ እየተነፈስኩ እንዲሁም እየሄድኩ ነው፡፡ ልትቀብሩኝ አትችሉም!"
"ምን አለ ውሳኔው ላይቀየር ተነስተህ ብትሄድ?"
"አልሄድም! በፍጹም አልሄድም! ከፈለጋችሁ ክሰሱኝ!" በላያቸው ላይ በሩን ዘጋ፡፡

የኮሚቴው አባላት መከሩ፤ "ምን እናድርግ?" ተባባሉ፡፡
"በቃ እርሱ እንዳለው ከስሰን ፍርድ ቤት እንገትረዋ!"
"ምን ብለን?"
"ይኽ ሰው ሞቶ ሳለ እምቢኝ አልቀበርም አለ ብለን"
"እሺ!!"
ሰውዬው አዘነ፡፡ በጠዋት እቤቱ መጥተው "ሞተሃል፤ እንቅበርህ!" ያሉት ሰዎች ሃሳብ እረፍት ነሳው፡፡ ከቤቱ ወጥቶ ወደ ራሱ ሰዎች ገሰገሰ፡፡ ሰበሰባቸውም፡፡

"ወገኖቼ!" አለ ሰውዬው፤ "ወገኖቼ! ጠዋት አንድ መርዶ ሰማሁ"
"የምን መርዶ?"
"ሞተሃል ተባልኩ፤ ተነስ እንቅበርህ! ተባልኩ"
"እንዴት?"
"እኔስ ግራ የገባኝ ምን ሆኖ?" ባዘነ ድምጽ ሰውዬው ተናገረ፡፡
ከመካከላቸው አንዱ ተነስቶ "በጭራሽ አይሆንም!! በጭራሽ! መቼም እኛ ወገኖችህ እያለን ይህ እኩይ እቅድ ይሳካል ብለህ አትስጋ" አለ፡፡ ቤቱ አጨበጨበ፡፡ ሰውዬው ይህ ሁሉ ወገን እንዳለው በማየቱ ደስ ተሰኘ፡፡ እፎይታም ተሰማው፡፡
ሰውዬው ተከሰሰ፡፡ ከከሳሾች መካከል ጥሩ አንደበት ያለው ሰው መናገር ጀመረ "ይህ ሰው የማይገባ ነውር ፈጽሟል፡፡ ለማህበረሰባችን ልማድ እና ክብር እንዲሁም ለእኛ ፍቅር ደንታ የለውም፡፡ በእርግጠኝነት ሞቷል!!" አስረግጦ ተናገረ፡፡
ዳኛው ዛሬ ገና አዕምሮአቸውን የሚፈትን ጉዳይ ገጠማቸው፡፡ "አንተስ ምን ትላለህ?" ተከሳሹን ጠየቁት፡፡ "ክቡር ሆይ!! እነሆ በፊትዎ ቆሜ እንደምን ይጠይቁኛል? ስለ እውነት በቁሜ ሞተሃል መባሌ ትልቅ በደል ነው፡፡"

"ተከሳሽ!"
"አቤት ክቡር ዳኛ!"
"ምስክር አለህ?"
"ለምኑ ክቡር ዳኛ?"
"ስላለመሞትህ!"
"ስላለመሞቴ ምን ምስክር ያስፈልጋል ክቡር ዳኛ!?"
"ነገር በሶስት ምስክር ይፀናል፡፡ ይኸው ነው፡፡"

ሰውየው ደነገጠ፡፡ ውሳኔውን ከወዲሁ ሲያስበው ዘገነነው፡፡ "በቁሜ ልትቀብሩኝ አትችሉም!! በጭራሽ አትችሉም!!" ሲል ጮኸ፡፡

"በላ ምስክር አምጣ!" ዳኛው መለሱ፡፡ ሰውዬው ፊቱን ወደራሱ ሰዎች ዞር ሲያደርግ ከከሳሾች ወገን ተቀምጠው ተመለከታቸው፡፡ ተስፋ ባለመቁረጥ የእያንዳንዳቸውን ስም እየጠራ ምስክር ይሆኑት ዘንድ ጠየቀ ነገር ግን የሁሉም መልስ "የለም! ሞተሃልና በውሽት አንመሰክርም!!" የሚል ሆነ፡፡
ዳኛውም ቁርጥ ያለውን ፍርድ አስቀመጡ "ይህ ሰው እንዳላችሁት ሞቷልና ወስዳችሁ ቅበሩት!!" ውሳኔያቸውንም በፊርማቸው አፀኑ፡፡
እኔም ዛሬ ይህን ተረት በመጠቀም የኢህአዴግን መሞት በሶስት ድርጊታዊ ምስክሮች ላረጋግጥ፡፡
1.      በመንግስት በአግባቡ ያልተጠና የሰፈራ ፕሮግራም ምክንያት ከቦታቸው ተፈናቅለው ሜዳ ላይ የወደቁ ገበሬዎችን ለመርዳት እንቅስቃሴ ያደረጉት አካላት ላይ የድብደባ እና የእስራት ተግባር መፈጸሙ
2.      በአሰቃቂ ሁኔታ 30,000 በላይ ዜጎቻችንን ህይወት ለቀጠፈው ግራዚያኒ ለተባለው የፋሽስት ኢጣሊያን ጦር አዛዥ የኢጣሊያ መንግስት ሃውልት ሊገነባለት አይገባም በማለት ተቃውሞ የወጡ ሰዎች ላይ ድብደባ፣ እንግልት እንዲሁም እስራት መፈጸሙ
3.      በቅርቡ ደግሞ በሳውዲ በስደት የሚኖሩ ዜጎቻችን ላይ የሚደረገው ከልክ ያለፈ እና አለም አቀፍ ህግጋትን የተላለፈ -ሰብዐዊ ድርጊት በመቃወም የሳውዲ መንግስት ከድርጊቱ እንዲታቀብ የታሰሩትም ባስቸኳይ እንዲፈቱ ብሎም ለሞቱ ወገኖቻችን ተገቢውን የደም ካሳ እንዲከፍል እንዲሁም የኢትዮጵያ መንግስትም ለዜጎቹ ተገቢውን ክብር በመስጠት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ወደ ሃገራቸው የመመለስ ግዴታውን በአግባቡ እንዲወጣ ለመጠየቅ የወጣ ህዝብ ላይ ድብደባ እና እስራት ማድረሱ
እነዚህ ከላይ የጠቀስኳቻ ነገሮች የኢህአዴግን ሞት ያስረዳሉ ብዬ ከማስባቸው እልፍ ምስክሮች መካከል የቅርብ ጊዜ ናቸው፡፡
ወያኔ መቼ ሞተ? ለሚለው ጥያቄ ትክክለኛውን ጊዜ መጥቀስ ባይቻልም አንዳንዶች ከመሪያቸው ሞት ጋር አብሮ ሞቷል ሊሉ ቢችሉም እኔ ግን ከዛም በፊት ነው ባይ ነኝ፡፡ ከዛ በፊት መቼ? ለሚለው ጥያቄ መልሱን ሊያመላክት ወይም ሊጠቁም የሚችለው በክፍፍላቸው ወቅት የቀድሞ መሪያቸው መለስ ዜናዊ "ከአናታችን ወይም ከጭንቅላታችን በስብሰናል!!" ብለው የተናገሩት ነው፡፡
መቼም አንድ ነገር አካሉ ከበሰበሰ (እጅ ወይም እግር ከሆነ) ተቆርጦ ይጣላል፡፡ የበሰበሰው ጭንቅላት ከሆነ ግን ህይወት የለውም ወይም ሞቷል ተብሎ ይታሰባል፡፡ ወያኔ ከዚህ የተፈጥሮ ህግ ውጪ ከሆነ እና እንደሌላው አካል ጭንቅላቱን አስቆርጦ ህይወት ከቀጠለ ወያኔ ማሰብ እና ማገናዘብ ላለመቻሉ ምክንያት ሊሆን ይችላል ነገር ግን እንደእኔ አመለካከት ወያኔ ያኔ ከክፍፍሉ በፊት ሞቷል፡፡ ስለዚህ ወያኔ ከዚያ በኋላ በነበሩት ጊዜያት እየታገለ የነበረው ላለመሞት ሳይሆን ላለመቀበር ነው፡፡
ስለዚህ ቀድሞ በየዘፈኑ መሃል
ቡና የለም እንጂ ቡናማ ቢኖር
አይ ሃገር አይ ሃገር አይ ሃገር ጎንደር፡፡
ይባል የነበረውን ተወዳጅ ግጥም እንዲህ ብዬ ለመቀየር አሰብኩ
ሕግ የለም እንጂ ህግማ ቢኖር
ዳኛም የለም እንጂ ዳኛማ ቢኖር
ፍርድ ቤት መገተር ወያኔን ነበር፡፡
በመጨረሻም የወገን ክብር ማለት የራስ ክብር እንዲሁም የሃገር ፍቅር ማለት የራስ ፍቅር ማለት ነው፡፡ ወገንን አዋርዶ እራስን ማስከበር አይቻልም፡፡ ባለቤት ቀንዱን የሰበረውን በሬ ጎረቤት አይኑን ያጠፋዋል እንደሚባለው እራሳችን ያዋረድነውን ሰው እንዲያከብርልን መጠየቅም አይቻልም፡፡ ህይወት ያለው ሰው ለሃገሩ ፍቅር እንዲሁም ለወገኑ ክብር ይኖረዋል፡፡ ታዲያ እውን ወያኔ የሚታገለው ላለመሞት ወይስ ላለመቀበር? እኔ ላለመቀበር ነው ብያለው እናንተስ?
ለመኖር ባደረገው ጥረት እራሱን የገደለ እንዲሁም ላለመቀበር በሚያደርገው ጥረት የራሱን ጉርጓድ የቆፈረ እንዲሁም በላዩ ላይ ትቢያ የነሰነሰ ከወያኔ ውጪ ማን አለ??? ማንም….      

የነገ ሰው ይበለን!!