Saturday, 5 April 2014

ዳግማዊ እምዬ ምኒልክ




መግቢያ
ወቅቱ ለረጅም ጊዜ መንግስታት ሲንቀሳቀሱበት የኖሩበትን በጉልበት ላይ የተመሰረተ የትክክለኛነት ማስረገጫ መርህ በመንግስታት መሃከል በተደረሱ ስምምነቶችና ህጋዊ ውሎች መተካት የተጀመረበት ነበር፡፡ የምዕራብ አውሮፓ መንግስታት በመሃከላቸው የነበረውን የእርስ በእርስ የቀኝ ግዛት ሽሚያ እና ግጭት በስምምነት ለመፍታት ውልና ቃል ኪዳን የገቡበት፣ የየራሳቸውን መንግስታት እና የግዛት ሉዓላዊነት አይገሰሴነት የተቀበሉበት ወቅት ነበር፡፡
በዚህ ወሳኝ የታሪክ ወቅት እንደ ሃገር መቆም ወይም አለመቆም፣ እንደ መንግስት መቆየት ወይም መጥፋት፣ እንደ አንድ ሃገር ህዝብ መኖር ወይም አለመኖር በሚል አጣብቂኝ ብዙዎቹ የተፈተኑበት ወቅት ነበር፡፡ በአፍሪካ እና በእስያ፤ እንደ ኢትዮጵያ የረጅም ዘመን እድሜ የነበረው ነፃ መንግስት እና ሃገር የነበራቸው ህዝቦች በአውሮፓውያን የቀኝ አገዛዝ ስር የወደቁበትም ወቅት ነበር፡፡ በተለይ አውሮፓውያኑ ሃያላን መንግስታት አፍሪካን ለመቀራመት በበርሊን ከተማ በ19ኛው ክፍለ ዘመን ማብቂያ ገደማ የደረሱበት የበርሊኑ ስምምነት እየተባለ በታሪክ የሚጠቀሰውን ሰነድ ከተፈራረሙ በኋላ የቅኝ ግዛት ማስፋፋት ተግባራቸውን በምድረ አፍሪካ አጣድፈው መላውን አፍሪካ በቅኝ ግዛት መዳፋቸው ሲያስገቡት፤ ኢትዮጵያ ብቻ፣ ዳር ድንበሯን እና የመንግስቷን ሉዓላዊነት ማስከበር የቻላች ነፃ ሃገር ሆና በታሪክ ፊት ወጣች፡፡
ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በምኒልክ የሚመራው የኢትዮጵያ መንግስት፤ በኢኮኖሚ እና በጦር ሃይላቸው ከኢትዮጵያ በብዙ ሺህ እጅ ይበልጥ የነበሩትን የአውሮፓ ሃያላን መንግስታት፤ የሃገራችንን መንግስት እና የዳር ድንበሯን ሉዓላዊነት እንዲቀበሉ ማድረግ ችሏል፡፡ ይህንን በይፋ እና በውስጠ ታዋቂነት ከአውሮፓዊያን ሃያላን ጋር የተደረሰን ስምምነት በመጣስ እና ኢትዮጵያንም በቀኝ ግዛቱ መዳፍ ለማስገባት የዘመተውን የኢጣሊያ ጦር አድዋ ላይ አይቀጡ ቅጣት በመቅጣት በአለም ላይ እየተከፈተ ለነበረው አዲስ ዘመን ኢትዮጵያን እና ህዝቦቿን ጠንካራ መደላድል ላይ አስቀምጧቸዋል፡፡
በኢትዮጵያ ዘመናዊ ታሪክ ውስጥ 1896 (እ.አ.አ) ታላቅ ትርጉም ያለው አመት ነው፡፡ ይህ ወቅት ኢትዮጵያ ራሷን ከጥቃት ተከላክላ እንደሃገር ክብሯን እና ነፃነቷን አስከብራ መቆም መቻልዋን ያስመሰከረችበት ነው፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ የኢትዮጵያ ህዝቦች በሙሉ በአንድነት እና በጋራ የተሳተፉበት የሃገር እና የነፃነት መከላከል እርምጃ የተወሰደበት ወቅት ነው፡፡
የእምዬ ምኒልክ ትሩፋቶች
ኢንሳይክሎፒዲያ ብሪታኒካ እምዬ ምኒልክን "ዘመናዊት ኢትዮጵያን የፈጠረ ሰው" ይላቸዋል፡፡ ጆን ማርካኪስ የተባለ ፀሃፊ ደግሞ አፄ ምኒልክ ለዘመናዊ ትምህርት ያበረከቱትን አስጠዋጽኦ ሲልገልጽ "ሚኒሊክ ዘመናዊ ትምህርት ቤትን በመክፈት በኢትዮጵያ ውስጥ ዘመናዊ ትምህርት ዘር የዘሩ ናቸው" በማለት ነው፡፡ ንጉሠ ነገሥቱ ያድዋ ጦርነት እስከ ተጀመረበት ጊዜ ድረስ ከውጪ ወራሪዎች ጋር በዲፕሎማሲያዊ መስክ እየተፋለሙ ከዚህ ጎን ለጎን ደግሞ ለዘመኑ ስልጣኔ በራቸውን በመክፈት የሚችሉትን ሁሉ አድርገዋል፡፡ ይህንንም ሲያደርጉ ከወግ አጥባቂ መኳንንት ጋር እየተጋጩ ነበር፡፡
በምኒልክ መሪነት፣ ልዩ ትዕዛዝ፣ ድጋፍ እና አስተዋጽዖ ወደ ሃራችን ከገቡ የቴክኖሎጂ ውጤቶች እና አገልግሎቶች መካከል ትምህርት፣ ባቡር (1893)፣ ስልክ (1882 ይህም ስልክ በተፈጠረ በ13 አመቱ ማለት ነው)፣ ፖስታ (1886)፣ ኤሌክትሪክ (1889)፣ አውቶሞቢል (1900)፣ ባህር ዛፍ (1886)፣ የውሃ ቧንቧ (1886)፣ ዘመናዊ ህክምና (1889)፣ ሆስፒታል (1890)፣ የመድሃኒት መሸጫ ሱቆች (ፋርማሲ፤ 1904)፣ ባንክ (1898)፣ ገንዘብ (1886)፣ ማተሚያ (1898)፣ ጋዜጣ (1900፤ አዕምሮ እና ጎህ ጋዜጣ)፣ ሆቴል (1898)፣ ሰንደቅ አላማ፣ ፖሊስ (ዘበኛ፤ 1901)፣ የፅህፈት መኪና (1887)፣ ሲኒማ (1889)፣ ወፍጮ (1835)፣ ጫማ፣ ድር፣ የሙዚቃ ት/ቤት (1887)፣ የሙዚቃ ሸክላ (1889)፣ ፍል ውሃ (1897)፣ ላስቲክ (1898)፣ ትንባሆ (1900)፣ መንገድ (1896)፣ አራዊት ጥበቃ፣ የጥይት ፋብሪካ (1899)፣ ብስክሌት (1893)፣ ቀይ መስቀል (1889)፣ እንዲሁም የሚኒስትሮች ሹመት (1900) ከብዙ ዋንኞቹ ናቸው፡፡  
እነዚህ የዘረዘርኳቸው አፄ ምኒልክ በዘመናቸው ወቅቱ ያፈራቸውን የቴክኖሎጂ ውጤቶች ወዳገራቸው ለማስገባት ጥረት ማድረጋቸውን ያሳያሉ፡፡ በመሰረቱ አጼ ምኒልክ ያከናወኗቸው ዘመን ተሻጋሪ የጥበብ ውጤቶች የተጠቀሱት ብቻ ነበሩ ማለት አይደለም፡፡ ከነዚህ ከላይ ከተዘረዘሩት የምኒልክ ትሩፋቶች ሁሉ በላይ ዋናው ግን የአድዋ ድል ነው፡፡ ኢትዮጵያዊነት ለነፃነቱ እና ለማንነቱ አይቀመሴ እና አይነኬ መሆኑን የተረጋገጠበት የነጮች የበላይነት ያበቃበት የታሪካችን ሁሉ ፈርጥ፤ አድዋ፡፡
ስለአድዋ ጦርነት ምን ተባለ?
"…ውጊያው  እስቲጀመር እንጠብቃለን፡፡ …እህቴ ሆይ ይህ ደብዳቤ ሲደርስሽ በሕይወት እንደሌለው ቁጠሪው፡፡ በሕይወት የምትቀሪው አንቺ እህቴ ለታዘዝኩት ስራ በክብር መሞቴንና በክብር መሞት ደግሞ ለሰው ልጅ አስፈላጊ መሆኑን መስክሪ፡፡ …" ካፒቴን ካኖቫቲ
"… በእንደዚህ አይነት ጭንቅ ጊዜ መልካም ምኞቴን ልገልጽልህ እወዳለሁ፡፡ … ጥቂት ሰዓት ከሚያስኬድ ርቀት ላይ ራሶች ተሰልፈዋል፡፡ ባንድነት ወደ እኛ ይጓዛሉ፡፡ ባታሊዮናችንም እንድናፈገፍግ ብቻ ይነግረናል፡፡ የዚህም ውጤት መጨረሻው ምን እንደሚሆን ይገባሃል፡፡ ጦሩ እየገፋ እስቲመጣ ብቻ እንጠብቃለን፡፡ … ለታዘዝነው ትዕዛዝ ህይወታችነን እንሰዋለን፡፡ የእኛ ነገር ተስፋ የሚያስቆርጥ ነው፡፡ አሁን ሁሉን ነገር ትቼ የማስበው ለተከበረው ሽማግሌ አባቴ እና ለተከበረችው እናቴ ነው፡፡ አንድ የምለምንህ ነገር አለኝ፡፡ ቤተሰቦቼን ምንም ነገር ቢያገኛቸው እንድትረዳልኝ አደራ እልሃለው፡፡ …" መቶ አለቃ ሚሴና
"ሃያ ሺህ ያህል ወታደሮች ያሉበት የኤሮፓ ጦር በአፍሪካ ሰዎች ለመጀመሪያ ጊዜ ተሸነፈ፡፡ በእኔ እምነት መሰረት በዘመናችን ታሪክ ውስጥ እንደ አድዋ ያለ ጦርነት የለም፡፡ በእልቂቱ በኩል 25,000 ሰዎች በአንዲት ጀምበር የሞቱበት እና የቆሰሉበት ነው፡፡ ፖለቲካ እና ታሪክ አበቃ፡፡ በአፍሪካ ውስጥ ታላቅ የተወላጆች ኃይል መነሳቱ ታወቀ፡፡ የአፍሪካ ተወላጆች ታሪክ ተለወጠ፡፡ ጥቁር በነጮች ላይ ሲያምፅ እና ሲያሸንፍ የመጀመሪያው መሆኑ ነው፡፡ አበሾች አደገኛ ህዝቦች መሆናቸውን ከኦሪት ዘፍጥረት ጀምሮ ተፅፎላቸዋል፡፡ የእኛ አለም ገና ቶር እና ኦዲዮን በሚባሉ አማልክት ሲያመልክ በነበረበት ጊዜ አበሾች የክርስትናን ሃይማኖት የተቀበሉ ናቸው፡፡ …አሁን የሁሉንም ፍላጎት አድዋ ዘጋው፡፡…" ቤርክሌይ፡፡
"…በጥጋባቸው አድዋ ላይ ተዋግተው ድል ሆኑ፡፡ እኔ ግን በድንቁርናቸው ብዛት የነዚያን ሁሉ ክርስቲያን ደም በከንቱ መፍሰሱን እያየሁ ድል አደረኳቸው ብዬ ደስ አይለኝም…"  እምዬ ዳግማዊ ምኒልክ
ምኒልክ እና ኤርትራ
አፄ ምኒልክ አጥብቀው የሚወቅሷቸው እና የሚያወግዟቸው የአሁኖቹ የኤርትራ ልጆች (ሻዕቢያ) እና የትግራይ ፋኖዎች (ህወሓቶች) ናቸው፡፡ ኢጣሊያኖች ባህረ ነጋሽን ከመረብ ምላሽ "ኤርትራ" ብለው በመሰየም የያዟት አፄ ዩሐንስ ራስ አሉላን ይዘው ወይም አግዘው ወደ መተማ በዘመቱበት ወቅት አጋጣሚውን በመጠቀም ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ በአፄ ዩሐንስ ዙፋን ወራሾች እና በንጉስ ምኒልክ መሀከል በተፈጠረ የስልጣን ሽኩቻ ምክኒያት ሁኔታዎች ስላገዟቸው ተደላድለው ለመቀመጥ ችለዋል፡፡
በኋላም ንጉስ ምኒልክ አፄ ቢሆኑም ቀሪዋን ኢትዮጵያ ይዘው አመቺ ጊዜ ከመጠበቅ ውጪ ሌላ አማራጭ አልነበራቸውም፡፡  እንዲያውም ለቀሪዋ ኢትዮጵያ በመስጋት ኢጣሊያኖች የመረብን ወንዝ ተሻግረው እንዳይወሯቸው የውጫሌን ውል መዋዋላቸው እውነት ነው፡፡ እንግዲህ ሻዕቢያ ሆነ ህወሐት የሚወነጅላቸው፡-
1.  "ከመረብ ወዲያ ያለውን አገር አገራቸው እንዳልሆነ በውል ፈርመው ለቀዋል" በማለት ነው፡፡ እነዚህ አካላት የወቅቱን የአለምን ተጨባጭ ሁኔታና የምኒልክን አቅም በቅጡ ያጤኑ አይመስሉም፡፡ ለነገሩ ቢያጤኑትም የመገንጠል እና የማስገንጠል መርህ ያነገቡ ስለሆነ ምኒልክን ለማውገዝ ምክኒያት ሆኗቸዋል፡፡ እውነታው ግን ዙሪያውን በቀኝ ገዢዎች ተከበው ሳሉ ኤርትራን ለማስለቀቅ ቢተነኩሱ ኖሮ መዘዙ ምን ሊሆን እንደሚችል ህሊና ያለው ሰው ሊገነዘበው ይችላል፡፡ በዚያን ጊዜ የነበራቸው አማራጭ ቀሪዋን ኢትዮጵያን ይዞ መቆየት ነበር፡፡ የዚህ እውነታ ማሳያ ኢጣሊያ ኤርትራ ላይ ተወስና መቅረት እንደማትፈልግ በውጫሌ ውል አንቀጽ 17 ምክኒያት አይቀሬውን ያድዋ ጦርነት ማስከተሉ ነበር፡፡
2.  ሌላውና ዋናው መወቀሻቸው ደግሞ "ያድዋን ድል እንደተቀዳጁ ወደ ፊት ቢገፉ ኖሮ ኢጣሊያኖችን ከኤርትራ ጠራርገው  ማባረር ይችሉ ነበር" የሚል ነው፡፡ እነዚህ ወገኖች ያልተገነዘቡት ወይም ለመገንዘብ ያልፈለጉት ነገር ቢኖር ድል ማድረግ እንዳለ ሁሉ መልሶ ድል መሆንም እንዳለም ነው፡፡
·         ኢጣሊያኖች ቢያንስ ከኢትዮጵያኖች የተሻለ የጦር መሳሪያ ነበራቸው፡፡
·         ሰራዊታቸውም የሰለጠነ ዘመናዊ ወታደር ነው፡፡
·         የስንቅ ድርጅታቸውም ለረጅም ጊዜ የሚቆይ ደረቅ ስንቅ ነው፡፡
·         ለቁስለኞች እና ለቀላል በሽተኞች የሚሆን መድሃኒት እና የህክምና ሙያተኞች ነበራቸው፡፡
ባንፃሩ ያፄ ምኒልክ ሰራዊት የታጠቀው መሳሪያ አንድ ጎረሰ ሲሆን በዚህ ላይ በዘመናዊ ውትድርና የሰለጠነ ሳይሆን በፍቃዱ የዘመተ የከተቴ ጦር ነበር፡፡ በሽታ ገብቶም እየጠረገው ነበር፡፡ የስንቅ አቅርቦቱም ባህያ እና ባጋሰስ የተጫነ ነው፡፡ ዝቅ ሲልም በሰው ትከሻ የተንጠለጠለ ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ያለው ደግሞ በየመንደሩ እየተመራ የሕዝብ ቀለብተኛ ሰራዊት ነበር፡፡ እንግዲህ ይህንን ሁሉ ችግር ተቋቁመው ኤርትራን ለማስለቀቅ ቢሞክሩ ኖሮ ያለ ጥርጥር ኢጣሊያ መልሶ የማይቃት እድሏ ሰፊ ነበር፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ ኢትዮጵያን ጠቅላ የመያዝ አጋጣሚው ከሰማይ የወረደ መና ነበር የሚሆንላት፡፡
ወረራ ወይስ አገር ማማከል?
አፄ ምኒልክ ሌላው የሚወቀሱበት በደቡብ፣ በምስራቅ እና በምዕራብ ኢትዮጵያ ባካሔዱት የግዛት ማስፋፋት ህይወት ጠፍቷል እንዲሁም ንብረት ወድሟል የሚል ነው፡፡ እንደ እውነት ከሆነ አገር ማማከል እና ወሰን ማስፋት በየትም አገር ተከናውኖ አልፏል፡፡ ኢጣሊያን ለማማከል ጋሪባልዲ፣ ጀርመንን ለማማከል ቢስማርክ አከናውነውት አልፈዋል፡፡ እንዲህ ሲኮንም ሁሉም ነገር አልጋ ባልጋ ሆኖ አይደለም፡፡ እልክ አስጨራሽ ጦርነቶች ተካሒደው እና አካል ጎድሎ፣ ንብረት ወድሞ፣ ህይወት ጠፍቶ እንጂ የመለኮት ፀበል እየረጩ ያገር ምክልና ተከናውኖ አይታወቅም፡፡ በዚህ አንጻር በዚያን ጊዜ አፄ ምኒልክ የወሰዱት እርምጃ አስፈላጊም፣ ተገቢም፣ ትክክልም ነበር ማለት ይቻላል፡፡
እሳቸው ያኔ አርፈው የያዙትን ይዘው በቸልታ ቁጭ ብለው ቢሆን ኖሮ እንግሊዝ ምዕራብ ኢትዮጵያን ጋንቤላን እና አሶሳን ከሱዳን ጋር እንዲሁም ደቡብ ኢትዮጵያን ከኬንያ ጋር ቀላቅላ ለመያዝ የሚሳናት ነገር አልነበረም፡፡ ምስራቅ ኢትዮጵያንም ቢሆን ከኢጣሊያ ጋር ተካፍላ እንደምትይዝ አይጠረጠርም፡፡ ይህ ቢሆን ኖሮ ደግሞ ዛሬ ሃረሬ እና ሶማሌ ክልሎች የሚባሉ ባልነበሩ ነበር፡፡
በመሰረቱ አፄ ሚኒሊክ የግዛት መስፋፋት ሲያደርጉ ቀድሞ የኢትዮጵያ አካል የነበሩትን እንጂ አዲስ አከባቢዎችን አልጨመሩም፡፡ በመሃከሉ የተበታተነች እና ኃይሏ የተዳከመች ኢትዮጵያን ነበር ከቅኝ ገዢዎች እየተከላከሉ ያጠናከሩት፡፡ ይህንኑ ተከትሎ ኢትዮጵያን በመቶ አመት ታሪክ በመከተር "አፄ ምኒልክ ናቸው ጠፍጥፈው የሰሯት" በማለት ያበሻ ቅኝ ገዢ አድርገው በመፈረጅ እኩል ከቅኝ ገዢዎች ጋር ማውገዝና ጥላሸት መቀባት ነው የተፈለገው፡፡ ይህንንም የሚያራግቡት የሻዕቢያ እና የህወሓት ከፍተኛ ያመራር አባላት ናቸው፡፡ ይህንኑ ተከትለው የኦነግ አባላትም የመገንጠል መርህ ነድፈው ለረጅም ጊዜ መንቀሳቀሳቸውና አፄ ምኒልክን ማውገዛቸው የአደባባይ እውነታ ነው፡፡ ከዚህ ላይ ግን ስንኩል አስገራሚ ነገሮችን አንስቶ ማየት ተገቢ ነው፡፡ እነሱም፡-
1.  ኢትዮጵያ የመቶ አመት ባለ ታሪክ ብሎ መፈረጅ እብደትም፣ ክህደትም፣ ቅዠትም ነው፡፡
2.  ኦነግ ልክ እንደ ሻዕቢያ የመገንጠል መርህ ይዞ በመነሳቱ አፄ ምኒልክን በቅኝ ገዢነት መፈረጁ ትልቅ ስህተት ብቻ ሳይሆን ትልቅ ጥፋትም ነው፡፡
የአፄ ምኒልክ ሞት
የአፄ ምኒልክ ህመም መነሻ የተላያዩ ሰዎች የተለያዩ ምክኒያቶች ቢሰጡጥም በወቅቱ ቤተ መንግስቱም አከባቢ ከመወራትም አልፈው የሚኒልክ ዶክተሮች በተደጋጋሚ የተናገሩት በጅሮንድ ሙልጌታ እና አዛዥ መታፈሪያ መርዝ እንዳበሏቸው ነው፡፡
ይህም ምኒልክ ጋር በደረሰ ጊዜ ንጉሱ ለህዝቡ "…ልጆቼን ያሳደኳቸውን  እና የማምናቸውን በጅሮንድ ሙልጌታን እና አዛዥ መታፈሪያን እንዳትነካብኝ፡፡ በክፉ አይንም አትይብኝ፡፡ መርዝ አብልተውኝ ከሆነ ነገሩ ከተጣራ በኋላ እኔው እቀጣቸዋለሁ፡፡ ነገሩ ተመርምሮ ሳይጣራ ግን በነሱ አትከፉብኝ፡፡ ቃሌን ጥሰህ ከድሮ ክብራቸው ብታዋርድብኝ ማርያምን አማላጅ የለኝም" የሚል አዋጅ አስነገሩ፡፡ ይህንን ተከትለው ህዝቡን ፈርተው ተደብቀው የነበሩት በጅሮንድ ሙልጌታ (የገንዘብ ሚኒስትር) እና አዛዥ መታፈሪያ (የግቢ ሚኒስትር) ከተደበቁበት ወጡ፡፡
ከጉዳዩ ጋር ንግስቲቱም ግኑኝነት አላቸው በመባሉ መኳንንቱ ለሁለት ተከፈሉ፡፡ ፊታውራሪ ሃብተጊዮርጊስ በጉዳዩ ላይ ለመወያየት ሚኒስትሮችን እና ጀርመናውያኑን ሰብስበው ውይይት እንዲያደርጉ አደረጉ፡፡ ጀርመኖቹም ለጉባኤው ሲናገሩ እቴጌ ጣይቱ ስልጣን ለመያዝ ሰለፈለጉ በጅሮንድ ሙልጌታ እና በአዛዥ መታፈሪያ በኩል ንጉሱን ሽባ የሚያደርግ መድሃኒት እንደሰጧቸው ተናገሩ፡፡ ከዚያም በኋላ ጉባኤው ምኒልክ አልጋ ወራሻቸውን እንዲያሳውቁ ወሰነ፡፡
ይህንኑ ውሳኔም ለምኒልክ አቀረበ፡፡ ምኒልክም የመጀመሪያ ኑዛዜያቸውን በደብዳቤ አጽፈው ሰጡ፡፡ ህዝቡ እና መኳንንቱ ጃንሜዳ ከተሰበሰበ በኋላ ግንቦት 10 ቀን 1901 ዓ.ም የኑዛዜው ቃል ተነበበ፡፡ እንዲህም ይል ነበር፡-
"የሃገሬ የኢትዮጵያ ልጆች፤ ልጆቼ እና ወዳጆቼ እግዚያብሄር የገለጠልኝን ምክር ልምከራችሁ፡፡ ምክሬንም እግዚያብሄር በልባችሁ ያሳድርላችሁ፡፡
አፄ ቴዎድሮስ የሞቱ ጊዜ ከእርሳቸው ጋር የነበረው ሰው ሁሉ ያንዱን ሃገር አንዱ እደርባለሁ ብሎ ሁሉም ላይረባ ተላልቆ ቀረ፡፡ ከዚያም በኋላ የአጼ ዩሐንስ ሰው የሆነውን የምታውቁት ነው፡፡ ባገር በሽታ ሳይገባበት፣ ሌላ የባዕድ ጦር ሳይነሳበት በምቀኝነት እርስ በእርሱ እንደተላለቀ አይታችኋል፡፡
አሁንም ልጆቼ፤ ወዳጆቼ አንዱ ባንዱ ምቀኝነት ይቅር፡፡ ያንዱን ሃገር አንዱ እኔ እደርባለሁ እንዳትባባሉ፡፡ እኔ እስካሁን በፍቅር እንዳኖርኳችሁ እናንተም በፍቅር እንድትኖሩ እለምናችኋለው፡፡ እናንተ አንድ ልብ ከሆናችሁ በምቀኝነት እርስ በእርስ ተዋግታችሁ ካላለቃችሁ በቀር አገራችንን ኢትዮጵያን ለሌላ ባዕድ አትሰጧትም፡፡ ክፉም ነገር ሃገራችንን አያገኛትም፡፡ ንፋስ እንዳይገባችሁ አገራችሁን በያላችሁበት በርትታችሁ ጠብቁ፡፡ ወንድሜ ወንድሜ እየተባባላችሁ ተደጋገፉ፡፡ የሃገራችንን ጠላት ተጋግዛችሁ ከድንበር መልሱ፡፡ የኢትዮጵያ ጠላት ባንዱ ወገን ትቶ በሌላው ወገን ቢሄድና ድንበር ቢገፋ በኔ ካልመጣ ብላችሁ ዝም አትበሉ፡፡
ይህንን ምክር ለእናንተ መስጠቴ፤ እኔማ በእግዚያብሄር ቸርነት ይህንን ያህል ገዝቼ የለምን ነገር ግን ሰው ነኝና እንግዲህ ስንት ያህል ዘመን እኖራለሁ ስል ነው፡፡ አሁንም እኔ እንደተመኘሁት እግዚያብሄር ከተጨመረበት እና ፍቃዱ ሆኖ ልጄን ቢያቆምላችሁ ከልጄ ጋር ሆናችሁ አገራችሁን ጠብቁ፡፡ አደራ ብያለሁ፡፡ አደራ የሚያኖሩበት ሰው የታመነ ነው፡፡ አሁንም እኔ እናንተን አምኜ ልጄን አደራ ብዬ እሰጣችኋለውና አሳድጉት፡፡ በብልሃት ምከሩት፡፡ በጉልበት አግዙት፡፡ ልጄን አደራ መስጠቴ ከልጄ ጋር ኢትዮጵያን በአደራ ጠብቁ ማለቴ ነው፡፡ እኔም ይኸው በገዢዎቹ አለማወቅ በህዝቡ አለመስማማት የተነሳ ከብዙ ዘመን ጀምራ ተከፋፍላ የነበረችውን አገራችንን ኢትዮጵያን ማስኜ ተጣጥሬ ይኸው አስፍቻታለሁ፡፡ እናንተም ከልጄ ጋር ሁናችሁ ተስማምታችሁ የኢትዮጵያን ድንበር እንዲሰፋ እንጂ አንድም ጋት መሬት እንዳይጠብ አድርጉ፡፡ ጠብቁ፡፡ አልሙ፡፡ የደጊቱ አገራችን የኢትዮጵያ አምላክ ያግዛችሁ፡፡ ይጠብቃችሁ፡፡
ከዚህ ቃል የወጣ በሰማይ ነፍሱ፤ በምድር ስጋው ከልጅ እስከ ልጅ ልጅ የተረገመ ይሁን፡፡ የኢትዮጵያ ውቃቢ ያጥፋው፡፡ እኔም ሳለሁ ከፍቃዴ የወጣውን እረግሜዋለሁ፡፡"
ይህንን ኑዛዜ ካስነገሩ በኋላ አፄ ምኒልክ በታላላቅ ስራዎች እና በፍርድ ላይ በመግባት ይከታተሉ ነበር፡፡ በመጨረሻም በታህሳስ 03 ቀን 1906 ዓ.ም በ69 አመታቸው በእለተ አርብ ሞቱ፡፡ ወዲያውኑ እንደሞቱ የግቢ ስራ ቤቶች የለቅሶ ድምጽ አሰሙ፡፡ ነገር ግን የልጅ እያሱ ባለሟሎች አገር እንዳይሸበር በቶሎ ዝም አሰኟቸው፡፡ ከዚህም በኋላ አፄ ምኒልክ በህይወት አሉ እየተባለና እየተወራ እስከ ሰገሌ ዘመቻ ድረስ ሁለት አመት ከአስር ወር ተደበቁ፡፡ የመንግስቱም ስራ በስማቸው ይካሔድ ነበር፡፡ በሚስጥርም ቢሆን ህዝቡ እና መኳንንቱ በተለያየ መንገድ ሃዘኑን ይገልጽ ነበር፡፡       
አርባ ስድስት አመት የገዛኸው ንጉስ
እንዳለህም ስጠኝ ከሌለህም ላልቅስ፡፡
በመጨረሻም ታሪክ መማር ለሁሉም ይበጃል፡፡ የቀደሙ ሰዎችን ስህተት እና በጎነትን አይቶ ለመንግስቱ እና ላገሩ የሚበጀውን ነገር ያውቅ ዘንድ ለቤተ-መንግስት ሰው ግን የግድ ያስፈልጋል፡፡ የታሪክ ትምህርት ግን የሚጠቅመው እውነተኛ የታሪክ ትምህርት ሲሆን ነው፡፡ እውነተኛም ነገር ለመፃፍ ቀላል አይደለም፡፡ የሚከተሉት ሶስት ተሰጦዎች ያስፈልጉናልና፡፡ መጀመሪያ የተደረገውን ለማስተዋል ተመልካች ልቦና፤ ሁለተኛ የተደረገውን ለመፍረድ የማያዳላ አእምሮ፤ ሦስተኛ  የተመለከቱትን እና የፈረዱትን ለማስታወቅ የጠራ የቋንቋ አገባብ ያስፈልጉናል፡፡ እነዚህ በሌሉበት ያለ ተመልካች ልቦና በሚያዳላ አዕምሮ የተፃፈ ታሪክ ትውልድን ወደ ተሳሳተ ጎዳና ይመራል፡፡ 
ምኒልክ የማንነታችን ተምሳሌት የነፃነታችን አርማ ናቸው!!
የምኒልክን 100 የሙት አመት ምክኒያት በማድረግ ተዘጋጀ!!

ምንጭ፡-
·         በሙት መንፈስ አገር ሲታመስ በአንዳርጌ መስፍን
·         ነፃነት የማያውቁ ነፃ አውጪዎች በአንዳርጋቸው ጽጌ
·         ነጋድራስ ገብረ ህይወት ባይከዳኝ ሥራዎች
·         አጤ ምኒልክ በጳውሎስ ኞኞ

1 comment: